የዲፕሎማሲ መዲናዋ አዲስ አበባ 5ኛውን ዓለም አቀፍ የአፍሪካ የሕዝብ ጤና ጉባኤን እንድታስተናግድ በይፋ ተመረጠች። የአፍሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያና መከላከል ማዕከል (Africa CDC) ኢትዮጵያን የመረጠው ያላትን የላቀ የማስተናገድ አቅምና ዘመናዊ የ”ስማርት ሲቲ” መሰረተ ልማት ከግምት ውስጥ በማስገባት ሲሆን፣ በዚህ ታላቅ ጉባኤ ላይ ከ30,000 በላይ ተሳታፊዎች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ከተማዋ በቅርቡ ካስተናገደችውና በስኬት ከተጠናቀቀው 38ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ እንዲሁም ከተለያዩ ዓለም አቀፍ የንግድና የቴክኖሎጂ ፎረሞች በመቀጠል፣ ለዚህ ዓለማቀፍ የጤና ጉባኤ መመረጧ የአዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተመራጭነት ይበልጥ አጽንቶታል። መዲናዋ በዚህም ለዲፕሎማሲያዊ ስብሰባዎች ብቻ ሳይሆን ለታላላቅ ሳይንሳዊና የጤና ኮንፈረንሶች ያላትን ዝግጁነት በተግባር አረጋግጣለች።
