የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 17ኛ መደበኛ ስብሰባው በኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ መንግስትና በፈረንሳይ የልማት ኤጀንሲ መካከል የተፈረመውን የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጅ መርምሮ አጸደቀ፡፡
የብድር ስምምነት አዋጁን አስፈላጊነት አስመልክተው የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ ምህረቱ ሻንቆ (ዶ/ር) በሰጡት ማብራሪያ ብድሩ የኢትዮጵያ መንግሥት የጀመረውን የአገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ዕቅድ ለመደገፍ የሚያግዝ የቀላል ብድር ስምምነት መሆኑን አስረድተዋል።
አክለውም የገንዘብ ድጋፉ መንግሥት እያከናወነ ያለውን ስር ነቀል የኢኮኖሚ ለውጥ ፣ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የኢነርጂ ዘርፍ እንቅስቃሴዎችን ለማገዝ የሚውል እና ብድሩ በቀጥታ ወደ መንግሥት ግምጃ ቤት የሚፈስ፣ ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና የመንግሥትን የበጀት አቅም ለማጠናከር ታስቦ የቀረበ ነው ብለዋል።
የብድር ስምምነቱ የወለድ መጠን በዓመት 1.1በመቶ ዝቅተኛ ወለድ የሚታሰብበት፣ 0.5 በመቶ የአገልግሎት ክፍያ የሚፈጸምበት እና የ5 ዓመት የችሮታ ጊዜን ጨምሮ በ15 ዓመታት ውስጥ ተከፍሎ የሚጠናቀቅ መሆኑም ተመላክቷል፡፡
ምክር ቤቱም የብድር ስምምነቱ ከኢትዮጵያ የብድር ስትራቴጂ ጋር የተጣጣመና በክፍያ ረገድ ጫና የማይፈጥር በመሆኑ እና መንግሥት የገቢ አሰባሰብን ለማሳደግ፣ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋትና መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የጀመረውን ጥረት ይበልጥ እንደሚያግዘው በማንሳት ረቂቅ አዋጁን አዋጅ ቁጥር 1414/2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡
