የካይሮ የወንጀል ችሎት፤ ዕውቋን የቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጅ ሳራ ካሊፋን ጨምሮ በ12 ሰዎች ላይ በተደራጀ የዕፅ ዝውውር መሳተፋቸው በመረጋገጡ የስቅላት ሞት ፍርድ አስተላለፈ።
ለመንግሥት ውግንና ያለው አል-አህራም እንደዘገበው፤ ፍርድ ቤቱ የሞት ፍርዱን ያሳለፈው ተከሳሾቹ አደንዛዥ ዕፆችን ለማምረት የሚያገለግሉትን በማስገባትና በማሰራጨት የተደራጀ የቪዲዮ ወንጀል ቡድን አቋቁመዋል በሚል ነው።
በዚሁ መዝገብ በተካተቱ ሌሎች ዘጠኝ ተከሳሾች ላይ የእድሜ ልክ እስራት የተፈረደ ሲሆን፣ ሰባት ተከሳሾች ደግሞ ነፃ ተብለዋል። በአጠቃላይ መዝገቡ 28 ተከሳሾችንና ከ750 ኪሎ ግራም በላይ አደንዛዥ ዕፆችን ያካተተ ነው።
የ39 ዓመቷ ሳራ ካሊፋ፤ “ሚሽን ኢምፖሲብል” በተሰኘው የጸጥታና ወንጀል ነክ ፕሮግራሟ የምትታወቅ ሲሆን፣ የፕላስቲክ ቀዶ ሕክምና ክሊኒክና የዝግጅት ማስተባበር ኩባንያ ባለቤት ነበረች። በተጨማሪም በኢንስታግራም ገጿ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ተከታዮች አሏት።
ሳራ የቀረበባትን ክስ አስተባብላ “በሕይወቴ ሲጋራ እንኳ አጭሼ አላውቅም” በማለት ንፅህናዋን ለመርማሪዎች ተናግራለች። በፍርድ ቤት ችሎት ወቅትም እያለቀሰች “እባክዎን ያዳምጡኝ፤ ወላጆቼ በስርዓት ነው ያሳደጉኝ፣ ሶላት የሚሰግዱ ሰዎች ናቸው፤ የዕፅ ገንዘብ አያስፈልገኝም” በማለት ምህረት ጠይቃለች።
ዓቃቤ ሕግ እንደገለጸው፤ ቡድኑ ከውጭ አገር ጥሬ ዕቃዎችን በማስገባት በመኖሪያ ቤቶች ውስጥ ሰው ሰራሽ ዕፆችን ያመርት የነበረ ሲሆን፣ አባላቱም ዕቃዎችን በማስገባት፣ በማምረትና በማሰራጨት ተግባር ተከፋፍለው ይሠሩ ነበር። ከዕፁ በተጨማሪ ፈቃድ የሌላቸው የጦር መሳሪያዎችና ጥይቶች ተይዘዋል።
የሞት ፍርዱ የተላለፈው የግብፅን ጠቅላይ ሙፍቲ ሃይማኖታዊ አስተያየት ከተጠየቀ በኋላ ሲሆን፣ ውሳኔው በይግባኝ ሰበር ችሎት ሊቀየር ይችላል። ሳራ ካሊፋ በቁጥጥር ስር የዋለችው እ.አ.አ. በወርሃ ሚያዚያ 2025 ሲሆን፣ በፍርድ ቤቱ በሌላ መዝገብ አሽከርካሪዋን በመደብደብና በመቅረጽ የ3 ዓመት እስራት ተፈርዶባታል።
