የአዲስ አበባ ምግብ መድሃኒት ባለስልጣን በትምህርት ቤቶች ዙሪያ የትንባሆ ምርቶች መሸጫ ክልከላ ርቀት ወደ 500 ሜትር ከፍ መደረጉን አስታውቋል፡፡
እርምጃው ህፃናትና ወጣቶችን ከትንባሆ ጭስና ሱስ አደጋ ለመከላከል እንዲሁም በትምህርት ቤቶች አካባቢ ጤናማ እና ንፁህ አካባቢ ለመፍጠር የተወሰደ የጤና ጥበቃ ፖሊሲ መሆኑ ተጠቅሷል።
አዲሱ ደንብ የትንባሆ ምርቶች በትምህርት ቤቶች በቅርብ ርቀት ላይ እንዳይገኙ በማድረግ የህፃናት መጋለጥን ለመቀነስ ያለመ ሲሆን እርምጃው በተለይም በተማሪዎች ዘንድ የትንባሆ ምርት መዳረሻን ለመገደብ እና የሱስ መጀመሪያ ዕድሜን ለመቀነስ የሚያግዝ መሆኑ ተነግሯል።
በተጨማሪም በተካሄደ ሰፊ የቁጥጥር ዘመቻ 1.3 ሚሊዮን ሕገወጥ ሲጋራዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸው ተገልጿል። ይህ እርምጃ በገበያ ውስጥ የሚሰራጩ ሕገወጥ የትንባሆ ምርቶችን ለመቆጣጠር የተደረገ የሕግ ማስከበር እንቅስቃሴ አካል ነው ተብሏል፡፡
በደንቡ መሠረት ትንባሆን የተከለከሉ ቦታዎች ላይ ሲሸጥ የተገኘ ማንኛውም ግለሰብ እስከ 6 ወር ቀላል እስራት ወይም እስከ 5,000 ብር የሚደርስ የገንዘብ ቅጣት ሊጣልበት እንደሚችል ተጠቁሟል።
የባለሥልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ሙሉ እመቤት ታደሰ እንደገለፁት ይህ የቁጥጥር እርምጃ በከተማ አስተዳደሩ የጤና ፖሊሲ አቅጣጫ መሠረት በተደረገ ውሳኔ መተግበሩን አስረድተዋል።
ህብረተሰቡ የትንባሆ ቁጥጥር ሕጎችን በማክበር ከጭስ ነፃ፣ ንፁህና ጤናማ የከተማ አካባቢ ለመፍጠር ከመንግስት አካላት ጋር እንዲተባበር ጥሪ ቀርቧል።
