ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ያለውን የፀጥታ ሁኔታ ለመገምገም ያለመ መድረክ ተካሄዷል።
መድረኩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከባለድርሻዎች ጋር የፀጥታ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ያዘጋጀው መሆኑ ተመላክቷል።
በመድረኩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤን ጨምሮ የክልሎች ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የፀጥታ አካላትና የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ተገኝተዋል።
የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላተወርቅ ኃይሉ በዚህ ወቅት እንዳሉት÷ ምርጫ ቦርድ ባወጣው የጊዜ ሠሌዳ መሠረት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።
በዚህም ከጥር 1 ጀምሮ እስከ የካቲት 1 ቀን 2018 ዓ.ም በሚቆየው የዕጩዎች ምዝገባ እስካሁን 41 በተናጠል እና 15 በሦስት የተለያዩ ጥምረቶች የቀረቡ ፓርቲዎች ዕጩዎቻቸውን በመመዝገብ ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
ምርጫው በሚደረግባቸው አካባቢዎች ያለውን የፀጥታ ሁኔታ በአረንጓዴ፣ ቢጫና ቀይ የተለየ ሲሆን÷ በመድረኩ እነዚህ የፀጥታ ሪፖርቶች ቀርበው ከባለድርሻ አካላት ግብአት ይሰጥባቸዋል ሲሉ ተናግረዋል።
የፀጥታ ሁኔታ ተለዋዋጭ እንደመሆኑ በአንድ መድረክ ብቻ እንደማይቋጭ የጠቀሱት ሰብሳቢዋ÷ በየጊዜው በሚኖሩ አዳዲስ ሁኔታዎች ተመስርቶ ለምርጫው የሚደረገው ዝግጅት እንደሚቀጥል መናገራቸውን የዘገበው ኤፍ ኤም ሲ ነው።
ቀደም ሲል ቦርዱ የዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ መስጫ ቀን ባሳወቀበት መዳረክ ላይ ለምርጫው አስቻይ ሁኔታ ስለመኖሩ ተጠይቀው ማብራርያ የሰጡት የቦርዱ ዋና ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ አስቻይ ሁኔታ በአንድ ቀን፣ በሶስት ቀን፣ በአምስት ቀን የሚሰራ አይደለም ቀጣይነት ያለው እና እስከ ምርጫው ዕለት ድረስ የሚከናወን ስራ ነው ማለታቸው የሚታወስ ነው።
በወቅቱ አስቻይ ሁኔታ ሲባል የፀጥታ ሁኔታዎች ብቻ አለመሆናቸውን የገለፁት ሰብሳቢዋ መሬት ላይ ያለውን የፖለቲካ ምህዳርን እንደሚያካትት ገልፀዋል። በዚህም ፓርቲዎች እንደልባቸው ይንቀሳቀሳሉ ወይ የሚለውም ላይ ቦርዱ ዕለት ዕለት እየሰራበት መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል።
