በማህበራዊ ሚዲያዎች የሚሰራጩ ሀሰተኛ የባህል ሕክምና ማስታወቂያዎች

Date:

የተለያዩ ሀሰተኛ ሥሞችንና አድራሻዎችን በመጠቀም በማህበራዊ ሚዲያዎች የሚሰራጩ የባህል ሕክምና ማስታወቂያዎችን ለመቆጣጠር ከአቅሙ በላይ መሆናቸውን የአዲስ አበባ ባህል ሕክምና አዋቂዎች ማህበር አስታውቋል።

በማህበሩ ሥር የሚገኙ ከ130 በላይ የባህል ሐኪሞች ሕጋዊ ፈቃድ አውጥተው በከተማዋ ዘርፈ ብዙ አገልግሎትን እየሰጡ እንደሚገኝ የገለጹት፤ የማህበሩ ፕሬዝዳንት መጋቢ ጥበብ መርጌታ መንግስቱ ደስታ ናቸው።

የተለያዩ ወረቀቶችን እየለጠፉ ማስታወቂያ የሚያስነግሩ አካላት ከአዲስ አበባ ምግብና መድኃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን ጋር በጋራ በመሆን እና በደንብ ማስከበር አማካኝነት እርምጃም እንዲወሰድባቸው በማድረግ ድርጊቱ እየቀነሰ መምጣቱን ተናግረዋል።

ከዚህ ባሻገር በማህበራዊ ሚዲያ የሚሰራጩት ሀሰተኛ ማስታወቂያዎችን ለመቆጣጠር ከአቅም በላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።

እነዚህ ግለሰቦች በሥማቸው ያልተከፈተ ስልክ ቁጥር እና የባንክ አካውንት በመጠቀም እንዲሁም፤ ትክክለኛ አድራሻን ሳያስቀምጡና ሕጋዊ ፈቃድ ሳይኖራቸው እንደሚሰሩ ተናግረዋል።

ነገር ግን የተጭበረበሩ ግለሰቦችን በመያዝና ማስታወቂያዎችን በመለየት ለመንግሥት ተቆጣጣሪ አካላት መረጃ በማድረስ ተይዘው ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ለማድረግ በጋራ እንደሚሰራበት አንስተዋል።

በማህበሩ የሕግ አገልግሎትና ሰነዶች ኮሚቴ ኃላፊ ሐኪም ታምራት ተስፋፅዮን በበኩላቸው፤ “መርጌታ” የሚለውን ቃል እና የማህበሩ ኃላፊዎችን ሥምና ፎቶዎችን በመጠቀም በማህበራዊ ሚዲያ በርካታ ሀሰተኛ መረጃዎችን እያሰራጩ የሚገኙ ግለሰቦች መኖራቸውን ገልጸዋል።

“ይህ ደግሞ ማህበረሰቡ የተዛባ አመለካከት እንዲኖረው አድርጎብናል” ብለዋል።

በዚህ ሂደትም ትልቁ ችግር ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ያለን ግለሰብ ማንነቱን አለመለየት መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ ሲደወልላቸውም ስልክ የማያነሱ መኖራቸውን ተናግረዋል።

ማህበሩ በስሩ የሚገኙ አባላት ላይ ጥብቅ ክትትል እንደሚያደርግ ያነሱት ሐኪም ታምራት፤ ከማህበሩ ውጪ ያሉትን ደግሞ ለሚመለከታቸው የሕግ አካላት ጥቆማ እንደሚሰጥ ገልጸዋል።

ሙያው ሳይኖራቸው ነገር ግን ባለሙያ መስለው በመግባት በተሳሳተ መንገድ የሚጠቀሙ ሰዎች በሁሉም ክልሎች መኖራቸውን የሚያነሱት ደግሞ፤ የማህበሩ የፕሮጀክትና ፕሮግራም ማስተባበሪያ ኃላፊና የመድኃኒት ባለሙያ ዳዊት ዲቀሶ ናቸው።

ይህም ትልቁ የዘርፉ ችግር መሆኑን በመግለጽ፤ የምዝገባ ስርዓቱን በማሻሻልና የቁጥጥር ሂደቱን በማጠናከር መንግሥት በዋናነት መሰራት እንደሚጠበቅበት ጠቁመዋል።

ከዚህ በተጨማሪ ማህበሩ ለሙያ ማህበራት በተሰጡ ኃላፊነቶች አማካኝነት በራሱ የሥነ-ምግባር ኮድ (መመሪያ) መሰረት ተገቢ ያልሆኑ ማስታወቂያዎችን ማስነገርን ጨምሮ ሕገ-ወጥ የሆኑ አሰራሮችን እንዳከተሉ ቁጥጥር እንደሚደረግ ተናግረዋል፡፡

(አሐዱ ሬዲዮ)

ያጋሩ!

መጽሔቶች

በብዛት የተነበቡ

ተጨማሪ ጽሑፎች
ተመሳሳይ

ሳፋሪኮም በኢትዮጵያ ለሚገኘው ቅርንጫፉ ተጨማሪ 1.4 ቢሊዮን ሺሊንግ ኢንቨስት አደረገ

የኬንያው የቴሌኮም ግዙፍ ኩባንያ ሳፋሪኮም እስከ ሰኔ 2018 ዓ.ም...

በምክክሩ ሕዝበ ውሳኔ የተጠየቀባቸው ጉዳዮች

በሀገራዊ የምክክር ጉባኤ 15ኛ ቀን ውሎ “ስልታዊ” ቡድኖች በተጠናቀሩ...

ንባብ ለሕይወት ባዛር እየተካሄደ ነው !!!

በንባብ ለሕይወት ፕሮጀክትና በኢትዮጵያ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት አዘጋጅነት የሚካሄደው...

በኢራን የኤነርጂ መሠረተ ልማቶች ላይ ያነጣጠረ አዲስ መጠነ ሰፊ ጥቃት መታቀዱ ተሰማ

የአሜሪካ ጦር በዚህ ሳምንት መጨረሻ በኢራን ላይ አዲስ ጥቃት...