በኢትዮጵያ የመጀመሪያው LEGO የሕጻናት መጫወቻ ዕቃዎች መሸጫ መደብር ተከፍቷል። በመደብሩ ለሽያጭ የቀረቡ የመጫወቻ ዕቃዎች የሕጻናትን የፈጠራ አቅም የሚያሳድጉ ናቸው ተብሏል።
ዛሬ አራት ኪሎ በሚገኘው አምባሳደር ሞል፣ ሶስተኛ ፎቅ ላይ ተመርቆ ስራውን የጀመረው የተለያዩ የLEGO ምርት የሆኑ የሕጻናት መጫወቻ ዕቃዎችን የያዘው መደብሩ፣ ከዕቃዎች ሽያጭ ባሻገር ሕጻናት የቡድን ስራ እና ጥበባዊ አገላለጾችን በጨዋታ ማሰስ የሚችሉበት የመማሪያ ማዕከል ስለመሆኑ ተነግሯል።
በምረቃ መረሐ ግብሩ ላይ ጨዋታ ዓለምአቀፋዊ ቋንቋ ስለመሆኑ ሲነገር፣ ይህ የLEGO መደብር ዓለምአቀፋዊውን ቋንቋ ለየት ባሉ አማራጮች ለኢትዮጵያ ሕጻናት ለማስተዋወቅ ጥረት እንደሚደረግ ለማወቅ ተችሏል።
የሴቶች እና ማሕበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ፣ በኢትዮጵያ የዴንማርክ አምባሳደር ሱኔ ክሮግስትራፕ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ዕንግዶች በምረቃ መረሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ነበር።
LEGO ተቀማጭነቱን በዴንማርክ ያደረገ የሕጻናት መጫወቻ ማምረቻ ድርጅት ሲሆን፣ በዓለምአቀፍ ደረጃ በተለያዩ አገራት የሕጻናት የመዝናኛ መንደሮችን ገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት በማድረግ የሚታወቅ ነው።
