የካቲት ላይ በተፈጸመው የመጀመሪያ ጥቃት ለተገደሉት የቀድሞው ጠቅላይ መሪ አያቶላህ አሊ ኻሜኒ መንግሥታዊ የቀብር ሥነ ሥርዓት ለማካሄድ እየተዘጋጀች ያለችው ኢራን፤ አሜሪካ እና እስራኤል ማንኛውም ጥቃት እንዳይሰነዝሩ አስጠነቀቀች።
የቀድሞው ጠቅላይ መሪ የቀብር ሥነ ሥርዓት ከሐሙስ እስከ ቅዳሜ ድረስ በኢራን እና ኢራቅ ውስጥ የተለያዩ ስፍራዎች እንዲካሄድ ዝግጅት እየተደረገ ነው። በተለያዩ ደረጃዎች ያሉ የበርካታ አገራት ባለሥልጣናትም በሥነ ሥርዓቱ ለመታደም ወደ ቴህራን እንደሚጓዙ አስታውቀዋል።
ቻይና፣ ፓኪስታን፣ ሕንድ እና ኳታር ባለሥልጣናቶቻቸውን ከሚልኩ አገራት መካከል ተጠቅሰዋል። ጦርነቱን ለመቋጨት አሸማጋይ የሆነችው የፓኪስታን ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ የአያቶላህ ኻሜኒን ቀብር ለመታደም ወደ ኢራን እንደሚጓዙ መንግሥታቸው ገልጿል።
ለቀብር ሥነ ሥርዓቱ ወደ ኢራን ለሚመጡ “ሁለት ሺህ” የአፍጋኒስታን ዜጎች ቪዛ እንደተሰጠም ቢቢሲ ፐርሺያ ምንጮችን ጠቅሶ ዘግቧል።
ይህ ዝግጅት እየተካሄደ ባለበት ወቅት ኻታም አል አንቢያ በመባል የሚታወቀው የኢራን ጦር ሠራዊት ማዕከላዊ ማዘዣ የማስጠንቀቂያ መግለጫ ማውጣቱን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።
ዋና አዛዡ አሊ አብዶላህ በመንግሥት መገናኛ ብዙኃን በተላለፈ መግለጫቸው፤ “የኢራንን ጠላቶች በተለይም አሜሪካን እና ጽዮናዊውን ሥርዓት (እስራኤል) ከማንኛውም የተሳሳተ ስሌት እንዲቆጠቡ” አስጠንቅቀዋል።
“አገራችን ላይ ለሚቃጣ ማንኛውም ስጋት እና ጥቃት በጦር ኃይሎቻችን ስለሚሰጠው ከባድ የአጸፋ እርምጃ እንዲያስቡ እናስጠነቅቃለን” ሲሉም አሳስበዋል።
ረቡዕ ዕለትም የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፤ በአገሪቱ ሕዝብ ወይም አመራር ላይ ለሚሰነዘር ማንኛውም ስጋት አፋጣኝ እና ጠንካራ ምላሽ እንደሚሰጥ በመግለጽ ተመሳሳይ ማስጠንቀቂያ ሰጥተው ነበር።
አራግቺ ይህንን ማስጠንቀቂያ የሰጡት የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር ኢዝራኤል ካትዝ የአሁኑ የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ “ለሞት የታጩ ናቸው” የሚል አስተያየት ከሰጡ በኋላ ነው።
በቀብር ሥነ ሥርዓቱ ወቅት ከፍተኛ የደኅንነት እርምጃዎች እንደሚተገበሩ እንዲሁም በበርካታ ከተሞች ጊዜያዊ የአየር ክልል እገዳ እንደሚጣል መገለጹን ሮይተርስ ዘግቧል።
