የቀድሞው የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ እና የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አባል አቶ ታዬ ደንደአ እጃቸው ላይ ካቴና ለማስገባት ፈቃደኛ ባለመሆናቸው በፍርድ ቤት ቀጠሯቸው ላይ ሳይገኙ ቀሩ።
አቶ ታዬ ደንደአ ረቡዕ ታኅሣሥ 22/2018 ዓ.ም. ልደታ በሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የቀረቡባቸውን ሦስት ክሶች ለማየት ቀጠሮ ተይዞላቸው ነበር።
ፍርድ ቤቱ ቀጠሮ ይዞ የነበረው የዐቃቤ ሕግን ክስ እና የተከሳሹን ተቃውሞ ለመስማት ነበር።
ይሁን እንጂ የአቶ ታዬ ደንደአ ጠበቆች በችሎቱ ላይ ቢገኙም እርሳቸው ግን ሳይገኙ ቀርተዋል።
የማረሚያ ቤቱ የፖሊስ መኮንኖች ለችሎቱ አቶ ታዬ ደንደአ እጃቸው ላይ ‘ሰንሰለት ለማድረግ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው’ ፍርድ ቤት እንደማያቀርቡ ተናግረዋል።
አቶ ታዬ ቀደም ሲል በአለርጂ ምክንያት ሰንሰለት ማድረግ እንደማይፈልጉ ተናግረው ነበር።
ፍርድ ቤቱ በበኩሉ የማረሚያ ቤት ፖሊስ ተከሳሹን በ’ጥቃቅን ምክንያቶች’ ወደ ፍርድ ቤት አለማቅረቡ ስህተት መሆኑን ተናግሯል።
ችሎቱ አቶ ታዬ ደንደአ ሐሙስ ታኅሣሥ 23/2018 ዓ.ም. ችሎት ፊት እንዲቀርቡ ትዕዛዝ ሰጥቷል።
አቶ ታዬ ከቀረቡባቸው ሦስት ክሶች በሁለቱ ነጻ ሲባሉ የጦር መሣሪያ ሕግን በመተላለፍ በቀረበባቸው ክስ ግን ጥፋተኛ ተብለው የሰባት ዓመት ከሁለት ወር እስር ተፈርዶባቸዋል።
አቶ ታዬ ነጻ የተባሉባቸው ክሶች “ከጠላት ጋር ማበር” አና የአገር መከላከያ ሠራዊትን ለመምታት “ዝግጅት አድርገዋል” የሚሉት ሁለት ከባድ ክሶች ናቸው።
