“ነጭ የላስቲክ ሳህን ፊት ለፊቴ ተቀምጧል… ከትሪው ላይ ከሳህኑ ጎን ጠይም ድፍን ዝቡቅቡቅ እንጀራ እንደ ቱባ ተጠቅልሎ ተጋድሞአል፡፡ የወሰን እናት ከጓዳ ባለ አበባ ጎድጓዳ ሳህን ይዘው መጡና ለወሰን አቀበሉዋት፡፡ … ጎድጉዋዳው ሰሀን በአበባ ስዕል ባሸበረቀ እፊያ ተከድኖአል፡፡ በእፊያውና በሳህኑ ከንፈሮች መሀል ብር መሰለ የሚያበራ ጭልፋ ወደ አየር ውስጥ ተዘርግቷል:: ወሰን እፍያውን ስትከፍተው ዐይኖቼን ወደ ጎድጓዳው ሳህን ሆድ ዕቃ ወረወርኩ፡፡ ታላቅ ቀይ ወጥ አየሁ፡፡ ንጉሠነገሥት ኃይለሥላሴ፣ ደጃዝማች ክፍሎም፣ አፈንጉሥ ዘለቀ፣ አባ ጆቢር፣ አባ ጅፋር የሚባሉት የሚበሉት ዐይነት ቀይ ወጥ፡፡ የተጌጠ ጠይም ደም ይመስላል፡፡ በቅባት የሰከረ፡፡ ከዚህም ሰካራም ወጥ ደካማ ጢስ ቀስ እያለ ወደ ላይ ይነሳል (ምን አድርጌው ነው እንዲህ በቀስታ የሚነሳው? ልቤን ሊሰልበው ነበርን?)፡፡”
አዳም ረታ፣ ግራጫ ቃጭሎች
ይህን ያውቁ ኖሯል?
ኢትዮጵያ ውስጥ በዓመት 58 ሺህ ሰዎች በልብ ህመም ምክንያት ሕይወታቸው እንደሚያልፍ የጥናት ውጤት አመላክቷል፡፡ በዚህ ጥናት ውጤት መሰረት በየስምንት ደቂቃው የአንድ ሰው ሕይወት ያልፋል ማለት ነው፡፡ የዓለም የበሽታዎች ጫና ጥናት በፈረንጆቹ 2019 የሠራው ጥናት ውጤት እንዳሳየው በኢትዮጵያ 2 ነጥብ 8 በመቶ ያህሉ ወይም ከ2 ሚሊየን በላይ ሰዎች የልብ ህመም አለባቸው፡፡
ሥነ-ግጥም
ትዝታ፡-
አጁ ቢጠነክር ቢመክት ጎራዴ
ሰውነት ስጋዬ ስቃይን ቢቋቋም ችሎ ቢኖር ሆዴ፣
ያ ብሩህ አንጎሌም በዕውቀት ማር ሰክሮ
የሕይወትን ቀለም ለራሱ አስተምሮ
መኖር አውቆበታል ተላምዶ ከኑሮ፡፡
ምስኪኑ ልቤ ግን!
ጿካማው ልቤ ግን በአንቺ ተንገላቶ
የመፋቀር አምላክ አንቺ አዳልቶ
ታስጋልቢኝ ጀመር የትዝታ ፈረስ እስኪነጋ መሽቶ፡፡
የግጥም ጥም፣ ሳልሳዊ አስፋው ከበደ
አማርኛ አባባሎች
- ለዋንጫ ቡሽ ለውሀ ጉሽ የለውም፤
- የሌባን ጠበቃ ደርበህ ውቃ፤
- ተዋጊ በሬህን ተናካሽ ውሻህን ያዝ፤
- ፈጣሪን የሚያህል ጌታ ርስትን ያህል ቦታ፤
- ከአፍ የወጣ ቃል ከእጅ የወደቀ እንቁላል፤
- ሳይቃጠል በቅጠል፤
- ድሀ በሽታ አያውቅም ሀብታም ጤና የለውም፤
- ለወጡም እዘኑለት ከደረቁም ብሉለት፤
- ሀምሌን በብጣሪ ነሀሴን በእንጥርጣሪ፤
አማርኛ አባባል
