ኩል የፋሽን ዲዛይን፤ የሜካፕ እና የሞዴሊንግ ማሠልጠኛ ተቋም ላለፉት 12 ወራት ያሠለጠናቸው ከ200 በላይ የሚሆኑ ሠልጣኞቹን ለአራተኛ ጊዜ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የኢንዱስትሪ ባለቤቶች፤ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ አርቲስቶች፣ የተማሪ ወላጆች በተገኙበት በጦርሃይሎች መኮንኖች ክበብ ዛሬ መጋቢት 27 ቀን 2017 ዓ.ም በድምቀት አስመርቋል።
በውድድሩ ላይም አንድ አካል ጉዳተኛ ኢትዮጵያዊ እና ሁለት ስደተኛ የሆኑ የመናዊና ኤርትራዊ ሴቶች ያለባቸው ችግር ሳይበግራቸው ከሌሎቹ እኩል ስራቸውን መድርክ ላይ አቅርበዋል።
በምርቃት ስነ-ስርዓቱ ላይ የተመረጡ 28 የሚሆኑ ተመራቂዎች በባህላዊና በዘመናዊ መልኩ በውብ ዲዛይን የተሠሩ የተለያዩ የብሔር ብሔረሰቦችን ባህሎች የሚገልፁ አልባሳቶችን ኢንተርናሽናል መድረኮች ላይ በሚሰሩ ታዋቂ ሞዴሎች ተለብሶ የፋሽን ሾው ውድድር የተካሄደ ሲሆን ውድድሩንም ታዋቂ ዲዛይነሮችና ታዋቂ አንጋፋ አርቲስቶች ዳኝተውታል፡፡
ተቋሙ ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን የኩል የፋሽን ዲዛይን፤ የሜካፕ እና የሞዴሊንግ ማሠልጠኛ ተቋም ባለቤት እና መስራች የሆኑት አቶ እሸቱ ደጉ የተናገሩ ሲሆን በተጨማሪም ከተለያዩ የመንግስት፣ የግል እና ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት የተለያዩ ሀገራት ስደተኞች፣ ከስደት ተመላሾች እና አካል ጉዳተኛ ሴቶችን በነፃ እያሰለጠኑ እንደሚገኝ ገልፀዋል።
ኩል የፋሽን ዲዛይን፤ የሜካፕ እና የሞዴሊንግ ማሠልጠኛ ተቋም በሙያው ላይ ከፍተኛ እውቀትና ልምድ ባላቸው ባለሙያዎች የተቋቋመና በቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ዘርፍ የአጫጭር ጊዜ ስልጠናዎችን ለህብረተሰቡ ለመስጠት ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርትና ስልጠና ጥራት ቁጥጥር ባለስልጣን ሙሉ እውቅና ወስዶ ለረዥም አመታት በተለያዩ ቦታዎች የስልጠና መስጫ ማእከላትን ከፍቶ እውቅና ባገኘባቸው ዘርፎች ስልጠናዎችን በመስጠት ላይ የሚገኝ ተቋም ነው።
