የኢራን መገናኛ ብዙኃን የአገሪቱ ጦር የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም መቆጣጠር እንደጀመረ መግለጹን ዘገቡ።
ፋርስ የዜና ወኪል፣ የኢራን የተማሪዎች ዜና ወኪል እንዲሁም ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃኑ ኢሪብ አብዮታዊ ዘቡን ጠቅሰው የወሽመጡ አካባቢን ጦሩ ተቆጣጥሮ “በቀደመ ሁኔታው ላይ” መመለሱን ዘግበዋል።
የተወሰኑ የጭነት መርከቦች በወሽመጡ በኩል ማለፍ ችለው ነበር።
አብዮታዊ ዘቡ በመግለጫው አሜሪካን “በባሕር ላይ ውንብድና” ወንጅሎ “እገዳ የምትለው” ከባሕር ላይ ዘረፋ አይተናነስም ብሏል።
ኢራን ቀደም ሲል ወደቦቿ ተዘግተው የሚቆዩ ከሆነ ወሽመጡን እንደምትዘጋ ዝታ ነበር።
የሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን በስተደቡብ የሚገኝ ጠባብ መተላለፊያ ሲሆን የዓለም 20 በመቶ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ይጓጓዝበታል።
ኢረን ከአሜሪካ ያደረገችው ድርድር ያለ ስምምነት መጠናቀቁን ተከትሎ የአሜሪካ ጦር ወደ ኢራን ወደቦች መርከቦች እንዳይገቡ እና እንዳይወጡ ለማድረግ እገዳ ጥሏል።
የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ግን እገዳው ካልተነሳ ሆርሙዝን እንደሚዘጉ ሲያስጠነቀቅቁ ቆይተዋል።
BBC
