የኢትዮጵያ ሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች በሀገር ውስጥ አቅም ላይ በመመስረት ለሀገርና ለህዝብ ተጠቃሚነት እንዲሰሩ የሚያስተባብር ግብረ ሃይል መቋቋሙን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን አስታወቀ።
ግብረ ሃይሉ የተቋቋመው ከተለያዩ የሃይማኖትና የፋይናንስ ተቋማት እንዲሁም ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በተወጣጡ አባላት መሆኑ ተገልጿል።
የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካው ሞላ የቡድኑን ዋና ዓላማ በተመለከተ ሲናገሩ፤ “ዓላማው የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራዎችን በመስራት በሀገር ውስጥ አቅም የተገነባ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት መፍጠር ነው” ብለዋል፡፡
ድርጅቶቹ ከሌሎች ተቋማት ጋር ተቀናጅተው እንዲሰሩ ለማስቻል ግብረ ኃይሉ የተለያዩ ተግባራትን እንደሚያከናውንም አስረድተዋል።
በተለይም ድርጅቶቹ በሀገር ውስጥ የተመሰረተ አቅም እንዲኖራቸውና ወደ ተግባር እንዲገቡ የሚረዱ የፖሊሲ፣ የአሰራር እና የህግ ጉዳዮችን የማስተባበር ኃላፊነት ለዚህ ቡድን መሰጠቱን ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
የግብረ-ኃይሉ መቋቋም ቀጥተኛ የሀብት ማሰባሰብ ዓላማ ባይኖረውም፣ ድርጅቶቹ በሀገር ውስጥ አቅም ላይ በመመስረት ውጤታማ እንዲሆኑ እንደሚያግዝ ተጠቅሷል።
በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ 8 ሺህ 400 የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የሚንቀሳቀሱ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ 65 በመቶ የሚሆኑት በስራቸው ላይ ለውጥ ዕያሳዩ እንደሆነ ተነግሯል።
አሐዱ ሬዲዮ
