የተፈናቃዮችን ጉዳይ ለፖለቲካ ዓላማ ማዋል ሰብአዊ መብትን መሸርሸር ነው ሲሉ በትግራይ ክልል የሚንቀሳቀሱት ትግራይ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ (ትዴፓ) እና የባይቶና አባይ ትግራይ ገለጹ።
ፓርቲዎቹ “ከተለያዩ አካባቢዎች ተፈናቅለው በክልሉ በሚገኙ መጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ የሚገኙት ከ1 ሚልዮን በላይ የሀገር ውስጥ ፍልሰተኞች ጉዳይ ለፖለቲካ ፍጆታ መዋሉ ተፈናቃዮቹ ማግኘት የሚገባቸውን ጥቅም እንዳያገኙ ከማድረጉም በላይ በሰዎች ሰብአዊ መብት ላይ ቁማር መጫወት ነው” ብለዋል።
“በክልሉ የሚገኙ ፖለቲከኞች የፍልሰተኞቹን ጉዳይ የውዝግብ እና ክርክር መነሻ ማድረጋቸው ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ነው” ያሉት የትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ትዴፓ) ሊቀ መንበር ዶ/ር አረጋዊ በርኸ ናቸው።
ዶ/ር አረጋዊ በተጨማሪም “ቅድሚያ ለሰብዓዊ መብት መሰጠት ቢኖርበትም፤ በተለይም በክልሉ ተሰሚነት ያለው ህወሃት ትግራይ ተፈናቃዮችን መጠቀሚያ እያደረጋቸው ነው” ሲሉ ከሰዋል።
“ተፈናቃዮች የፖለቲካ መጫወቻ ካርድ መሆን የለባቸውም። ተፈናቃዮች ከፖለቲካ ውጪ ናቸው። ሰብአዊ እርዳታ ከሁሉም ነገር ሊቀድም ይገባል” ብለዋል።
“አንደኛው የህወሓት ቡድን ‘ተፈናቃዮች ካልተመለሱ ትጥቅ አልፈታም’ ሲል በተደጋጋሚ መደመጡ ተፈናቃዮቹን የፖለቲካው አካል የማድረግ ሐሳቡ ማሳያ ነው” ያሉት ሊቀ መንበሩ፤ “ትጥቅ መፍታት እና ከተፈናቃዮች ጋር የሚገናኝ ነገር አይደለም” በማለት ተናግረዋል።
የባይቶና አባይ ትግራይ ፓርቲ ሊቀመንበር ክብሮም በርኸ በበኩላቸው በክልሉ የሚንቀሳቀሱ በርካታ ፓርቲዎች እንዳሉ ገልጸው፤ “ለተፈናቃዮቹ የተራዘመ ስቃይ እና ለፖለቲካ ፍጆቻ መዋል ዋነኛው ተጠያቂ ግን በክልሉ ተሰሚነት ያለው እንዲሁም የፕሪቶርያውን ስምምነት የፈረመው ህወሓት ነው” ብለዋል።
አክለውም “በክልሉ የምንቀሳቀስ ፖርቲዎች ተፈናቃዮች በዚህ ደረጃ ችግር ውስጥ እንዳይገቡ ተደጋጋሚ ጥረቶች ያደረግን ቢሆንም፤ ጥረታችን ሰሚ አጥቷል” ሲሉ ገልጸዋል።
“ህወሓት የስልጣን ግዜውን ለማራዘም ተፈናቃዮችንም መጠቀሚያ ከማድረግ ሊቆጠብ ይገባል” ብለዋል።
@አሐዱ
