በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀሱት ሁለቱም የቴሌኮም ኦፕሬተሮች ማለትም ኢትዮ ቴሌኮም እና ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፤ መንግሥት ባወጣው አዲስ ደንብ መሠረት የአገሪቱን የአደጋ መከላከል አቅም ለማጠናከር የሚውለውን የ5 በመቶ ክፍያ ተግባራዊ ማድረግ ጀምረዋል።
የቴሌኮም ዘርፉ ተዋናዮች የአደጋ ስጋት ፈንድ እንዲሰበስቡ የተወሰነ መሆኑ የሚታወስ ሲሆን ቅዳሜ ገበያ እንዳረጋገጠችው ኩባንያዎቹ ይህንኑ ግዴታ መወጣት ጀምረዋል፡፡
መንግሥት በአዋጅ ቁጥር 1386/2017 እና በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 576/2018 መሠረት፤ የአገሪቱን የአደጋ መከላከልና የመቋቋም አቅም በራስ አቅም ለመገንባት ከ17 የገቢ ምንጮች ቋሚ ሀብት ለመሰብሰብ መወሰኑ ይታወሳል።
ከእነዚህ የገቢ ምንጮች መካከል በቴሌኮም የድምፅና የዳታ አየር ሰዓት ሽያጭ ላይ የሚጣለው የ5 በመቶ ክፍያ አንዱ ሲሆን፤ ይህም በሁለቱም ኦፕሬተሮች አማካኝነት ከየካቲት ወር 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ መደረግ ጀምሯል።
ይህ የአደጋ ሥጋት ምላሽ ፈንድ አሰባሰብ በቴሌኮም ዘርፍ ላይ ብቻ የተገደበ ሳይሆን፤ ከባንኮች፣ ኢንሹራንስ፣ ነዳጅ ሽያጭ፣ ከአየር መንገድና ሌሎች የትራንስፖርት ዘርፎች፣ የንግድ ፈቃድ አገልግሎት እንዲሁም ሌሎችን አካቶ በጥቅሉ 17 የገቢ ምንጮችን የሚያካትት አገራዊ መርሃ ግብር ነው።
ፈንዱ በዋናነት በተፈጥሮና ድንገተኛ አደጋዎች ወቅት በውጭ ዕርዳታ ላይ ያለንን ጥገኝነት ለመቀነስና አገር በቀል የአደጋ መከላከያ አቅምን ለመገንባት የታሰበ መሆኑን መንግስት ማስታወቁ ይታወሳል፡፡
በመሆኑም ኢትዮ ቴሌኮም እና ሳፋሪኮም አዋጁን ተግባራዊ ማድረግ እንደጀመሩ የተሰማ ሲሆን፣ ከደንበኞቻቸው የአየር ሰዓትና የዳታ ግዢ ላይ የ5 በመቶ ክፍያን ለአገራዊ የአደጋ ሥጋት ምላሽ ፈንድ ጽሕፈት ቤት ገቢ የሚያደርጉ ይሆናል፡፡
