የሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን አሜሪካ በሩሲያ ሁለት ትላልቅ የነዳጅ ኩባንያዎች ላይ ማዕቀብ መጣሏን አጣጠጥለዋል፣ ይህንኑ ተከትሎ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንደተናገሩት የሩሲያው ፕሬዝዳንት በቅርቡ የኢኮኖሚውን ህመም እንደሚሰማቸው ጠቁመዋል።
ትራምፕ በዋይት ሀውስ ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት “እንዲህ አይነት ስሜት ስለሚሰማው ደስተኛ ነኝ” ብለዋል። “ይህ ጥሩ ነው ከስድስት ወር በኋላ ስለ ጉዳዩ አሳውቅዎታለሁ፤ ሁሉም ነገር እንዴት እንደሚሄድ እናያለን” ሲሉ ትራምፕ ተደምጠዋል፡፡
ፑቲን በትላንትናዉ እለት በግዙፎቹ የሩሲያ የነዳጅ ኩባንያዎች በሆኑት በሮስኔፍት እና ሉኮይል ላይ የተጣለውን ማዕቀብ “ወዳጅነት የጎደለው ድርጊት” ሲሉ ገልጸው ነገር ግን ድርጊቱ በሩሲያ ኢኮኖሚ ላይ የሚኖረውን ጉዳት አቅልለውታል።”በተፈጥሯቸው ማዕቀቦች ከባድ ናቸው እናም የተወሰነ ውጤት ይኖራቸዋል፤ ነገር ግን በኢኮኖሚያችን ጤና ላይ ምንም አይነት ተጽእኖ አይኖራቸውም” ሲሉ ፑቲን ተደምጠዋል፡፡
ዩናይትድ ስቴትስ ማዕቀቡን ረቡዕ እለት የጣለችው ሞስኮ በዩክሬን ያለውን ጦርነት ለማቆም የሰላም ሂደት ላይ “ከባድ ቁርጠኝነት ስለሌላት ነው” ማለቷ ይታወሳል፡፡
የግምጃ ቤት ዲፓርትመንት በመግለጫው እንዳስታወቀው እርምጃዎቹ የሩስያን የኢነርጂ ዘርፍ “የክሬምሊን ለጦር መሣሪያዎቿ ገቢ የማሳደግ አቅምን ለመጨመር” እና “የተዳከመ ኢኮኖሚዋን ለመደገፍ” ያነጣጠረዉን እንቅስቃሴ ይጎዳል ብሏል።የግምጃ ቤት ፀሐፊ ስኮት ቤሴንት በመግለጫቸው ላይ “ግድያውን ለማስቆም እና የተኩስ ማቆም እንዲደረስ ጊዜው አሁን ነው” ብለዋል።
#ዳጉ_ጆርናል
