የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት፣ ለጋዜጠኞች የሙያ ማረጋገጫ ለመስጠትና የጋዜጠኞች ምዝገባ ለማከናወን ውይይትና እንቅስቃሴ መጀመሩን ተከትሎ፤ የተለያዩ የሚዲያ ተቋማት፣ ጋዜጠኞችና የሙያ ማህበራት ጉዳዩን በተመለከተ የሕጋዊነት ጥያቄና ስጋቶቻቸውን በማቅረብ ላይ መሆናቸውን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን አስታውቋል።
ባለሥልጣኑ ባወጣው መግለጫ፤ የመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ጋዜጠኞችን ወይም የሚዲያ ባለሙያዎችን የመመዝገብም ሆነ የሙያ ማረጋገጫ የመስጠት ተግባርና ኃላፊነት በመገናኛ ብዙኃን አዋጅ ቁጥር 1238/2013 አልተሰጠውም ብሏል።
በመሆኑም የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን፣ ለዚህ የምክር ቤቱ ተግባር እውቅና እንደማይሰጥ አስታውቋል፡፡
