በአዲስ አበባ ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ ስድስት ካርል አደባባይ አካባቢ በሚገኝ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቅርንጫፍ አንድ ግለሰብ ሁለት ሰዎችን ገድሎ ራሱን ማጥፋቱ ተገልጿል ።
ድርጊቱ መጋቢት 2 ቀን 2017 ዓ.ም የፍቅር ጥያቄን አልተቀበልሽም በማለት በቅናት የፈተጸመ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኮማንደር ማርቆስ ታደሰ ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ተናግረዋል።
አቶ ሽፈራው ረጋሳ የተባለው ግለሰብ የፍቅር ጥያቄ ያቀረበላት ወይዘሪት ሃና ተስፋዬ የተባለች 32 ዓመት ግለሰብ የፍቅር ጥያቄ አቅርቦላት እንዳልተቀበለችው የተገለጸ ቢሆንም በድርጊቱ መንስኤ ዙሪያ አሁንም ምርመራው እየተጣራ መሆኑ ተገልጿል ።
ግለሰቡ በእለቱ ስራውን ጨርሶ የነበረ ቢሆንም ሌላ ሠራተኛን ተክቶ በመግባት ስራው ላይ ባለበት ሰዓት ሟች ሃና ልብስ ለመቀየር ስትገባ ሁለተኛ ሟች ንጉሴን ሰላም ስትለው በመመልከቱ ከምሽት የጥበቃ ሠራተኞች የጦር መሳሪያ በመቀበል ግድያውን መፈጸሙን ገልጸውልናል።
ግድያውን የፈጸመው ግለሰብ ባልደረባውን ተኩሶ ከገደለ በኋላ መሳሪያውን እንዲያስቀምጥ እና እጁን እንዲሰጥ በተደጋጋሚ ቢነገረውም አልሰማም ማለቱ ተገልጿል። በዚህም መካከልም ወደ ባንኩ አንደኛ ፎቅ በማምራት የፍቅር ጥያቄውን አልተቀበለችም ያላትን ወይዘሪት ሃና ልብሷን ልትቀይር በሄደችበት ተከትሎ በመግባት በጥይት መትቶ መግደሉን ፖሊስ ገልጿል።
ግለሰቡ ሁለቱን ባልደረቦቹን ከገደለ በኋላ በያዘው መሳሪያ የእራሱንም ሕይወት እንዳጠፋ የአዲስ አበባ ፖሊስ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኮማንደር ማርቆስ ጨምረው ለብስራት ሬዲዮ እና ቴሌቪዥን ተናግረዋል።
