በለሚ ኩራ ክ/ከተማ ወረዳ 3 ልዩ ቦታው ሰንሻይን ቤቶች ፊት ለፊት ከሚገኘው ውዳሴ ህንፃ ላይ ነዋሪ የነበረችው ሟች ወ/ሮ ቀነኒ አዱኛ ዋቆ መጋቢት 01 ቀን 2017 ዓ/ም ከሌሊቱ 10፡00 ሠዓት አካባቢ ከቤቷ የማብሰያ ክፍል በኩል ካለው በረንዳ 5ኛ ፎቅ ላይ ለጊዜው ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ ወድቃ ለህክምና እርዳታ ወደ ያኔት ሆስፒታል እየተወሰደች ባለበት ወቅት ህይወቷ አልፏል፡፡
የአዲስ አበባ ፖሊስ መረጃው ከደረሰው በኋላ የምርመራ ቡድን በማዋቀርና ቦታው ድረስ በመሄድ ተገቢውን የቴክኒክና የታክቲክ መረጃዎችን ያሰባሰበ ሲሆን የሟችንም አስከሬን ወደ ዳግማዊ ሚኒሊክ ሆስፒታል ለተጨማሪ ለምርመራ እንዲሄድ አድርጓል፡፡
ሟች ወ/ሮ ቀነኒ አዱኛ በወቅቱ ከበረዳ ላይ በወደቀችበት ሰዓት ፖሊስ በቤቱ ውስጥ የነበረውን ባለቤቷን ድምፃዊ አንዷለም ጎሳን በቁጥጥር ስር በማዋልም ምርመራ እያጣራ ሲሆን በቀጣይ የመጨረሻውን የምርመራ ውጤትም ለህዝብ ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል፡፡
በተለያዩ ማህበራዊ ድረ ገጾች ላይ ከፖሊስ የወንጀል ምርመራ ውጤት በፊት የሚናፈሱ መረጃዎች ተገቢነት የሌላቸው ከመሆኑም ባሻገር በምርምራ ሒደቱ ላይ የሚያሳድረውን አሉታዊ ተፅህኖ በመገንዘብ የተሳሳተ መረጃ የሚያስተላልፉ እና የሚያሰራጩ ግለሰቦች ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡ የአዲስ አበባ ፖሊስ አሳስቧል፡፡
