በኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ በዓለም መንግሥታት ጉባዔ ለመሳተፍ የተባባሩት አረብ ኢምሬቶች ገብቷል።
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ እና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህን ጨምሮ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችን ያካተተው ከፍተኛ ልዑክ ዱባይ ሲደርስ አቀባበል ተደርጎለታል።
“የወደፊት መንግሥታትን መቅረጽ” በሚል መሪ ሀሳብ ነገ በዱባይ በሚጀምረው የ2026ቱ የዓለም መንግሥታት ጉባዔ ከ150 በላይ ሀገራት የተውጣቱ የበርካታ ሀገራት መሪዎች እና ከ500 ያላነሱ ሚኒስትሮች ይሳተፉበታል።
ጉባዔው በሰው ሠራሽ አስተውሎት (አርቲፊሻል ኢንቴሊጀንስ) ልማት፣ በወደፊቱ የዘመናዊ ከተሞች እና መሠረተ ልማት ግንባታ እንዲሁም በዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ዙሪያ ይመክራል።
ፕሬዚዳንት ታየ በጉባዔው፥ ኢትዮጵያ በምሥራቅ አፍሪካ እየፈጠረችው ስላለው የኢኮኖሚ ትስስር፣ እያደረገችው ስለሚገኘው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲሁም ስላሏት የኢንቨትመንት ዕድሎች እና አማራጮች ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ያስረዳሉ።
ከጉባዔው ጎን ለጎንም ፕሬዚዳንቱ ከሀገራት መሪዎች ጋር የሁለትዮሽ ውይይት ያደርጋሉ።
ለ3 ቀናት በሚቆየው ጉባዔ የሳይንስ ሊቃውንትና የዓለም አቀፍ ተቋማት መሪዎች ለመጪው ዘመን የመንግሥታት አሠራር የመፍትሔ ሀሳቦችን እንደሚያቀርቡበት ተገልጿል።
