በአዲስ አበባ ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 07 በሚገኝ የገበያ ማዕከል ውስጥ፣ ለከፍተኛ የጤና ጉዳት ሊዳርግ የሚችል 90 ኩንታል የ“በሬዳ ባልትና” በርበሬ ገበያ ላይ ሳይሰራጭ መወገዱን የአዲስ አበባ ምግብና መድኃኒት ባለሥልጣን አስታወቀ።
ምርቱ በከፍተኛ ሁኔታ በአፍላቶክሲን (ሻጋታ) የተጠቃ ሲሆን፣ ይህም የሆነው አምራቹ 70 ኩንታል በርበሬ ላይ 20 ኩንታል ለውዝ በመቀላቀል እርጥበት ባለው መደብር ውስጥ በማከማቸቱ እንደሆነ ተገልጿል።
ይህ የተበከለ ምርት ለተለያዩ የካንሰር በሽታዎች የሚያጋልጥ በመሆኑ፣ ባለሥልጣኑ ምርቱ ወደ ህዝብ ሳይደርስ የማስወገድ እርምጃ ወስዷል። በድርጅቱ ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ የተወሰደ ሲሆን፣ በሰው ጤና ላይ አደጋ የደቀነው ግለሰብም ለሕግ አካላት ተላልፎ ተሰጥቷል። ድርጊቱ የተፈጸመው አላግባብ ትርፍ ለማግኘት በሚፈልጉ ስግብግብ ነጋዴዎች የሞራል ጉድለት መሆኑን የባለሥልጣኑ ኃላፊዎች ጠቁመዋል።
የአዲስ አበባ ምግብና መድኃኒት ባለሥልጣን መሰል የምግብ ክለሳና የባዕድ ነገር መቀላቀል ተግባራትን ለመከላከል ቁጥጥሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። ሕዝቡም ማንኛውንም የባልትና ምርቶች ሲገዛ ልዩ ጥንቃቄ እንዲያደርግና ጤናውን እንዲጠብቅ ጥሪ ቀርቧል።
