በኢትዮጵያ ለ3ኛ ጊዜ የሚከበረውን የዓለም የ‘ሴሬብራል ፓልሲ’ ቀንን ወይም በሕፃናት አዕምሮ ዕድገት ላይ በሚደርስ ጉዳት ምክንያት የሚከሰት፣ የእጅና እግር እንቅስቃሴን፣ የጡንቻን ጥንካሬ እና የሰውነት ሚዛንን የሚጎዳ የነርቭ ሕመም አስመልክቶ በመጪው ጥቅምት ወር ሀገር አቀፍ ንቅናቄና ታላቅ የእግር ጉዞ ሊካሄድ እንደሆነ የመርሃ-ግብሩ አዘጋጅ እዝነት አካል ጉዳተኛ ህፃናትና ወላጆች መርጃ ድርጅት አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ ነሐሴ 18 ቀን 2019 ዓ.ም. በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ሕዝባዊ የእግር ጉዞው ጥቅምት 8 ቀን 2019 ዓ.ም. “ለሲፒ ጉዳተኛ የነገ ተስፋ እጓዛለሁ” በሚል መሪ ቃል ይካሄዳል። የእግር ጉዞው መነሻውን ከፒያሳ ዓድዋ 00 በማድረግ እስከ ኩፓ ፓርክ ድረስ እንደሚዘልቅ ታውቋል።
የድርጅቱ መሥራች እና ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ዘቢባ አሕመድ በጋዜጣዊ መግለጫው ወቅት፣ የ’ሴሬብራል ፓልሲ’ ጉዳተኞችን አስመልክቶ ድምፅ ለመሆን በቂ እንዳልሆነ እና ግንዛቤውም እንዳልተፈጠረ አብራርተዋል።
‘ሴሬብራል ፓልሲ’ በሕፃናት አእምሮ ዕድገት ወቅት በሚደርስ ጉዳት ምክንያት የሚከሰት፣ የእጅና እግር እንቅስቃሴን፣ የጡንቻን ጥንካሬ እና የሰውነት ሚዛንን የሚጎዳ የነርቭ ሕመም ሲሆን፤ ችግሩ በአብዛኛው ከፅንስ ጊዜ ጀምሮ እስከ ሁለት ዓመት ዕድሜ ባለው ጊዜ ውስጥ ይከሰታል።
እንደ ሀገር በጉዳዩ ላይ በበቂ ሁኔታ ስላልተሰራበትና ጉዳቱ እየተባባሰ በመምጣቱ፣ የእግር ጉዞው ሰፊ ግንዛቤ ለመፍጠር ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ሥራ አስኪያጇ ገልጸዋል።
ሕብረተሰቡ ለዚሁ ተግባር የተዘጋጁ ቲሸርቶችን በመግዛትና በእግር ጉዞው በመሳተፍ ከተጎጂዎችና ከወላጆቻቸው ጎን እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል።
