በአፍሪካ የጤናውን ዘርፍ አቅም ለማጎልበትና ትብብርን ለመፍጠር ያለመው “ሜድ ኢድ አፍሪካ 2026” (MED ED AFRICA 2026) ዓለም አቀፍ ጉባኤ ከሰኔ 29 እስከ ሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም (July 6-8, 2026) በአዲስ አበባ ከተማ ለሦስት ቀናት እንደሚካሄድ የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።
በመድረኩ ከተለያዩ የአፍሪካ አገራት የተወከሉ የጤና ሚኒስትሮች፣ የፖሊሲ አውጪዎች፣ አካዳሚካውያን፣ ተመራማሪዎችና የዘርፉ አጋሮችን ጨምሮ ከ800 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚገኙ ተገልጿል።
“Preparing Africa’s Health Workforce for an Uncertain Future” በሚል መሪ ቃል የሚካሄደው ይህ ጉባኤ፤ የአመራር ብቃትን ማጠናከር፣ ቴክኖሎጂና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን (AI) ከሕክምና ትምህርት ጋር ማቀናጀት፣ የእናቶችና ሕፃናትን ጤና ጨምሮ ጤናማ አፍሪካን መገንባት፣ እንዲሁም የሴቶችን የውሳኔ ሰጪነት ሚና ማሳደግ በሚሉ አራት ዋና ዋና ነጥቦች ላይ ያተኩራል።
ጉባኤውን የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር ከኮምሳ (COMSA) እና ከግሎባል ሄልዝ ኢኩዊቲ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመሆን በዋና አዘጋጅነት የሚመራው ሲሆን፣ በሦስቱ ቀናት የምርምር ሥራዎችና ከ15 በላይ ድርጅቶች የሚሳተፉበት ኤግዚቢሽን ይካሄድበታል።
ኢትዮጵያ መድረኩን ማስተናገዷ በሕክምና ትምህርትና ልዩ ባለሙያዎችን በማፍራት ረገድ ያላትን ተሞክሮ ለማካፈል፣ የቱሪዝም ዘርፉንና ኢኮኖሚውን ለማነቃቃት፣ እንዲሁም የአገሪቱን ገጽታ ለመገንባት ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ጤና ሚኒስቴር አመልክቷል።
።
