በሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ሳቢያ ከመኖሪያ ቀዬአቸው ለተፈናቀሉ እንዲሁም የሰብዓዊ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ነዋሪዎች ድጋፍ ለማድረግ የአባላት ቁጥር ዝቀተኛ መሆንና የፋይናንስ ችግር ተግዳሮት እየሆነበት እንደሚገኝ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቀይ መስቀል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ለአሐዱ አስታውቋል።
በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች በሚባል ደረጃ ቀይ መስቀል ማኅበርን ‘በውጭ ድጋፍ የሚንቀሳቀስ የተራድኦ ድርጅት አድርጎ የማሰብ የተሳሳተ አመለካከት አለ’ የተባለ ሲሆን አባል የመሆን እና የአባልነት ክፍያ የመፈጸም ተነሳሽነት አለመኖሩም ተነግሯል።
በቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ የሰብዓዊ ዲፕሎማሲና ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ዳይሬክተር ሙሉዋስ አቲሳ በክልሉ 10 ሚሊዮን ገደማ የሚገመት ነዋሪ ቢኖረም የቀይ መስቀል አባላት ቁጥር ከ80 በመቶ በታች መሆኑን ለአሐዱ አብራርተዋል።
በመሆኑም የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ከአባላት በሚገኝ መዋጮ እና ከሌሎች ምንጮች በሚያገኘው ገቢ የሚተዳደር መሆኑን አውቆ ሁሉም ማኅበረሰብ አባል በመሆን እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል።
(አሐዱ ሬድዮ)
