ትምህርት ሚኒስቴር በሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ባከናወነው የትምህርት ማስረጃዎችን እውነተኛነት የማጣራት ሥራ፣ የ151 ሠራተኞች የትምህርት ማስረጃ ሐሰተኛ መሆኑን እንዳረጋገጠ አስታውቋል።
የሚኒስቴሩ የስትራቴጂክ ጉዳዮች ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ እሸቱ ገላዬ፣ “ኮሚሽኑ እንዲጣሩ ከላካቸው 38 ሺሕ 245 ማስረጃዎች መካከል እስካሁን የ34 ሺሕ 487ቱ የማጣራት ሥራ ተጠናቅቋል” ብለዋል።
በተከናወነው ማጣራት 33 ሺሕ 632ቱ መስፈርቱን አሟልተው ሲገኙ፣ 151ዱ ግን ሐሰተኛ መሆናቸው ተረጋግጦ ውድቅ ተደርገዋል ተብሏል።
በተጨማሪም የ694 ሠራተኞች የትምህርት ማስረጃ የሰነድ ጉድለት የታየበት ሲሆን፣ የቀሪዎቹ ሰራተኞች ማስረጃ በማጣራት ሒደት ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል።
ከሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ውጭም በሦስት የፋይናንስ ተቋማት የሚሠሩ 11 ሺሕ 600 ሠራተኞች ማስረጃ ተፈትሾ የሦስት ግለሰቦች ማስረጃ ሐሰተኛ መሆኑ ተረጋግጧል።
ሚኒስቴሩ ለሠራተኞች ምቹና ሳቢ የሥራ አካባቢን ለመፍጠር የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝም አቶ እሸቱ ገልጸዋል።
በሌላ በኩል፣ በኢትዮጵያ እና በሕንድ መካከል ያለው የትምህርት ትብብር መጠናከሩን ተከትሎ፣ በየዓመቱ ለ250 ተማሪዎች ነፃ የትምህርት ዕድል እየተመቻቸ ጅመሆኑ ተጠቁሟል። ይህም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ እንደሚያሳድገው ተገልጿል።
