በኢትዮጵያ የአቪዬሽን ዘርፍ ያለውን የሰው ኃይል ልማት ይበልጥ ለማሳደግና ዜጎችን በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመ የትብብር ስምምነት ተፈረመ። ስምምነቱ የተደረገው በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና በኢትዮጵያ አየር መንገድ መካከል ነው።
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ ይህ ትብብር የአየር መንገዱን የዳበረ የቴክኖሎጂና የሥልጠና ልምድ በመጠቀም ብቁ ባለሙያዎችን ለማፍራት የሚያስችል ነው። በተለይም በሚኒስቴሩ ሥር በሚገኙ የሙያና ቴክኒክ ሥልጠና ተቋማት በኩል የሚሰለጥኑ ወጣቶች በአቪዬሽን ዘርፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነታቸው እንዲረጋገጥ ትልቅ ዕድል ይፈጥራል።
በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ በዘርፉ ያለው የባለሙያዎች ፍላጎት ከፍተኛ በመሆኑ፣ ስምምነቱ ኢትዮጵያውያን በውጭ የሥራ ገበያ ውስጥ ተመራጭ እንዲሆኑ ያግዛቸዋል። በየዓመቱ በሺዎች የሚቆጠሩ የሥራ ዕድሎችን የሚፈጥረው የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ በዚህ ስምምነት አማካኝነት የሚፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል በበቂ ሁኔታ ለማግኘት እንደሚረዳውም ተመላክቷል።
ይህ ስምምነት በሀገሪቱ የሥራ አጥነት ችግርን ለመቅረፍና የሰለጠነ የሰው ኃይልን ለዓለም ገበያ በማቅረብ ረገድ የሚኖረው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑ በዕለቱ ተገልጿል።
