የሳይካትሪስት የሙያ ፈቃድና ሥልጠና የሌላቸው ግለሰቦች በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን የሚያስተላልፉት የተዛባ መልዕክት በታካሚዎች ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን የኢትዮጵያ የአዕምሮ ሕክምና ባለሙያዎች ማኅበር አስታውቋል።
የማኅበሩ የአባላት ጉዳይ ኮሚቴ ኃላፊና በኤካ ኮተቤ ሆስፒታል የአዕምሮ ሕክምና ስፔሻሊስት ዶክተር ኢማኑኤል አስራት ለአሐዱ እንደገለጹት፣ የሙያው ባለቤት ያልሆኑ አካላት ማኅበራዊ ሚዲያዎችን በመጠቀም ሕብረተሰቡን የሚያሳስት መረጃ እያቀረቡ ይገኛሉ።
የአዕምሮ ሕክምና ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚፈልግ ቢሆንም፣ ማኅበሩ ባደረገው ማጣራት ለሕክምና የማይመከሩ ምክሮችን የሚለዋወጡ አካላት መኖራቸውን አረጋግጧል።
በዚህም ሳቢያ በሰዎች ላይ ጉዳት እየደረሰ መሆኑን የሚገልጹ ተደጋጋሚ ጥቆማዎች ለማኅበሩ እየደረሱት መሆኑን ዶክተር ኢማኑኤል አብራርተዋል።
ማኅበሩ ሰሞኑን ባወጣው መግለጫ፣ እነዚህ የተዛቡ መረጃዎች ለሕክምና ስህተት የሚዳርጉ መሆናቸውን በማሳሰብ፣ በቀጣይ የሚዲያ ተቋማትንና ግለሰቦችን በስም ጠቅሶ ለሕግ ተጠያቂ እንደሚያደርግ አስታውቋል።
ይህንን የቁጥጥር እርምጃ ተግባራዊ ለማድረግ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በጋራ እየተሠራ ሲሆን፣ የጤና ባለሙያዎች የሚሰጡትን አገልግሎት ወሰን የሚለይ መመሪያ (Scope of Practice) ተዘጋጅቶ መጠናቀቁ ተገልጿል። ይህም የትኛው ባለሙያ ምን መሥራት እንዳለበት በግልጽ ለመለየት ያስችላል ተብሏል።
የአዕምሮ ሕክምና ስፔሻሊስት ለመባል ከ6 እስከ 7 ዓመታት የሕክምና ትምህርትና ተጨማሪ 3 ዓመታት በዘርፉ ስፔሻላይዜሽን መውሰድ እንደሚገባ የገለጹት ዶክተር ኢማኑኤል፣ ሕብረተሰቡ ባለሙያዎቹን በሪፈራልና በግል ሆስፒታሎች ማግኘት እንደሚችል ጠቁመዋል።
. (አሐዱ ሬዲዮ)
