በአዲስ አበባ ከተማ በተለይም በዋና ዋና መንገዶች ላይ የኮሪደር ልማቱን ከመጠበቅ አንፃር በርካታ ሥራዎች እየተሰሩ እንደሚገኝ የገለጸው የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን ወደ ፊት ምንም አይነት የእንስሳት እንቅስቃሴ እንዳይኖር ለማድረግ አጠናክሮ እንደሚሰራበት አስታውቋል።
በዚህም መሠረት በአሁኑ ወቅት በከተማዋ አገልግሎት ላይ ከሚውሉ እንስሳት አንዷ የሆነችውን አህያን በተመለከተ በኮሪዶር መንገዶች ላይ መንዳት የተከለከለ መሆኑን የባለስልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሻለቃ ዘሪሁን ተፈራ ገልጸዋል።
“ዘመን እየተሻሻለ ነው ድሮ በአህያ ነበር ጭነቶቻችንን የምንጭነው አሁን ደግሞ በተሽከርካሪ ነው” ሲሉ የገለጹት ዋና ሥራ አስኪያጁ አሁን ላይ ከተሽከርካሪም ደግሞ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ መምጣታቸውን አንስተዋል።
ስለዚህም ከተማ ከቴክኖሎጂ ጋር የተቀናጀ አሰራር እንጂ ወደኋላ ተመልሶ የቀሩ የትራንስፖርት አማራጮችን የሚጠቀምበት ሁኔታ እንደሌለ አፅንኦት ሰጥተዋል።
በመሆኑም በተለይም የኮሪደር ልማቱን አጠቃቀም ተከትሎ ለማህበረሰቡ በርካታ የግንዛቤ ማስጨበጫ መሰራቱን ገልጸው አውቆ የሚያጠፋ ካለ ግን የሕግ ማስከበር ሥራ እንደሚሰራ ተናግረዋል።
በዚህ ሂደት ውስጥም የቅጣት ደረጃዎችን መሠረት አድርጎ የሚወሰዱ እርምጃዎች መኖራቸውን አንስተው “የሚጣለው ቅጣት ግን አቅምን ያገናዘበ ነው” ብለዋል።
(አሐዱ ሬድዮ)
