አሐዱ ባንክ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን (ኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ) የሕንጻዎች አስተዳደር ኤጀንሲ ያበለጸገውን የዲጂታል ኪራይ አሰባሰብ ሥርዓት በይፋ ጀምሯል።
የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ቤቶች እና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ኤጀንሲ ይዞት የተነሣውን የዲጂታል አስተዳደር ግብ እውን ለማድረግ አሐዱ፡ባንክ ያበለጸገው ይህ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ሥርዓት፤ ብፁዕ አባታችን አቡነ ሳሙኤል በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የክርስቲያናዊ ተራድኦ ልማት ኮሚሽን እና ቤቶችና ሕንጻዎች አስተዳደር ልማት ኤጀንሲ የበላይ ጠባቂ ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት ዝርዝር ገለጻ ተደርጎበታል።
ይህ አዲስ የቴክኖሎጂ ሥርዓት ተከራዮች የኪራይ ክፍያቸውን በሞባይል ባንኪንግ በቀላሉ እንዲፈጽሙ የሚያስችል ሲሆን፣ የመክፈያ ጊዜ ማስታወሻና የክፍያ ምስጋና መልዕክቶችን በራሱ ይልካል።
በተጨማሪም የክፍያ ጊዜያቸው ያለፈባቸውን ተከራዮች የመቆጣጠር አቅም ያለው ሲሆን፣ ለቤተ ክርስቲያኗ ቀልጣፋ የፋይናንስ ቁጥጥርና ግልጽነትን ያሰፍናል ተብሏል።
