ኢትዮ ቴሌኮም በመጀመሪያው የሕዝብ አክሲዮን ሽያጭ የተረጋገጡ 45 ሺህ ባለአክሲዮኖች በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ፈቃድ ካላቸው ደላሎች ወይም የኢንቨስትመንት ባንኮች ጋር የንግድ አካውንት እንዲከፍቱ አሳሰበ።
ኩባንያው ይህን ጥሪ ያቀረበው በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ ላይ የንግድ ልውውጥ መጀመሩን ተከትሎ ነዉ።
የኩባንያው ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንደገለጹት፣ ብዙዎች አክሲዮኖቻቸውን መገበያየት ያልጀመሩት ስለ ካፒታል ገበያ አሠራር ያላቸው ግንዛቤ አናሳ በመሆኑ ነው።
በአሁኑ ወቅት የባለአክሲዮኖች ተሳትፎ በኩባንያው ላይ ብቻ ሳይሆን በደላሎች እና በኢንቨስትመንት ባንኮች ዙሪያ ባለው ሰፊ የገበያ ሥነ-ምህዳር ላይ የተመሠረተ መሆኑን ጠቁመዋል።
በመጀመሪያው ምዕራፍ የአክሲዮን ሽያጭ 47,377 እጩ ኢንቨስተሮች ተመዝግበው የነበረ ሲሆን፣ ወደ 10.7 ሚሊዮን አክሲዮኖች ተሸጠው 3.2 ቢሊዮን ብር ተሰብስቦ ነበር።
የሽያጭ ጊዜው ካበቃ በኋላ ከተቆጣጣሪ አካላት ጋር በመሆን በተደረገ የመረጃ ማጣራት፣ የደንበኛ ማንነት ማረጋገጫ እና የወረቀት የባለቤትነት መዝገቦችን ወደ ዲጂታል የመቀየር ሥራ ተከናውኗል።
