በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባለፉት ስድስት ዓመታት ከ23 ሺህ በላይ ሴት ተማሪዎችን ተጠቃሚ ያደረገው የኩሶ ኢንተርናሽናል ፕሮጀክት የማጠቃለያ መርሃ-ግብር ተካሄዷል።
በካናዳ መንግስት የገንዘብ ድጋፍ ሲተገበር የቆየው ይህ ፕሮጀክት፣ በክልሉ በሰባት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሚማሩ ሴት ተማሪዎችን ለከፍተኛ ትምህርትና ለተለያዩ የሥራ መስኮች ለማብቃት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል።
ፕሮጀክቱ የስርዓተ-ጾታ እኩልነትን ለማስፈንና ጾታዊ ጥቃትን ለመከላከል ካከናወናቸው ተግባራት በተጨማሪ፣ ለትምህርት ቤቶች 140 ኮምፒውተሮችን፣ የሶላር ኃይል አቅርቦት፣ ከ54 ሺህ በላይ አጋዥ መጻሕፍትና 4,500 ዴስኮችን በማቅረብ የመማር ማስተማር ሂደቱን አዘምኗል።
ከዚህም ባለፈ ፕሮጀክቱ የወላጆችን የኢኮኖሚ አቅም ለማሳደግ በሥራ ፈጠራና በመነሻ ካፒታል የደገፈ ሲሆን፣ በመተከል ዞን በጸጥታ ችግር የወደሙ ትምህርት ቤቶችን መልሶ በማቋቋም ረገድ አመርቂ ተግባራትን አከናውኗል።
የክልሉ ትምህርት ቢሮ አመራሮች ለተገኘው ውጤት ምስጋናቸውን አቅርበው፣ የተጀመሩ ስራዎችን በዘላቂነት ለማስቀጠልና ለወደፊትም ከድርጅቱ ጋር በአዲስ መርሃ-ግብር ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
