በግለሰብ ቤት ተቀጥረው የሚያገለግሉ የቤት ሠራተኞች ላይ ጥበቃና ደህንነት የሚሰጥ ሞዴል ሕግ ማዘጋጀቱን ፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ የተሰኘ ሀገር በቀል የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅት አስታውቋል።
ይህንን ሞዴል ሕግ በመንግሥት በግብዓትነት መውሰድ እንደሚችል ተገልጿል።
የቤት ሠራተኞችን ብቻ የሚመለከት ራሱን የቻለ ሕግ መውጣቱ የሚፈፀሙ ጥቃቶችንና የመብት ጥሰቶችን ለማስቀረት እንደሚያግዝ የገለጹት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር እና ተመራማሪ ዶ/ር ሰላም ኢሳያስ ናቸው።
ዶ/ር ሰላም አዋጁ ተግባር ላይ እንዲውል የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ በሚወጣበት ወቅት፤ በተቻለ መጠን የቤት ሠራተኞችን ሃሳብ ማካተት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
በኢትዮጵያ የቤት ሠራተኞችን የሚመለከት የተደራጀ ሕግ አለመውጣቱንና በፍትሃብሔር ብቻ የተቀመጠ ሕግ ስለመኖሩ የገለፁት ደግሞ፤ በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ በዓለም አቀፍ ሕግ ረዳት ፕሮፌሰር እና ተመራማሪ ሙሴ መዝገቡ ናቸው።
ረዳት ፕሮፌሰር ሙሴ እንዳሉት አዲሱ ሞዴል ሕግ የሠራተኞችን መብት እና ተጠቃሚነት የሚያስከብር፤ የአሰሪዎችን መብትም ታሳቢ ያደረገ ነው።
በመሆኑም “የኢትዮጵያ ቤት ሠራተኞች ጥበቃና ደህንነት” በሚል ስያሜ የተዘጋጀው ሕግ፤ የቤት ውስጥ ሠራተኞች በሳምንት የሚሰሩበትን ሰዓትና ከሥራ ሰዓት በላይ ከሰሩ ማግኘት ስለሚገባቸው መብት ይገልጻል።
ከዚህ በተጨማሪም ለሌሎች የመንግሥትና የግል ሠራተኞች ተፈፃሚ የሚሆነው የዝቅተኛ ደመወዝ ወለል የቤት ሠራተኞችንም እንዲመለከት እንደሚጠይቅ አሐዱ ሰምቷል።
የክፍያ ሁኔታ ቢያንስ በወር አንድ ጊዜ ሆኖ በጥሬ ገንዘብ እንደሚፈጸም እንዲሁም፤ የዓመት እረፍትና የሕመም ጊዜን ጨምሮ የመደራጀት መብትን የሚያስጠብቅ እንደሆነ ተነግሯል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
