በመካከለኛው ምስራቅ የተፈጠረው ቀውስ ተፅዕኖ ተከትሎ በሀገራችንና በዓለም ላይ ነዳጅን በገበያ ላይ ለማግኘት አስቸጋሪ እየሆነ መመምጣቱን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክ ሚኒስትር ዴዔታው በርሆ ሀሰን ለኤን ቢሲ ኢትዮጵያ ተናግረዋል።
ቀውሱ ኢትዮጵያ ነዳጅ በምታጓጉዝበት የባህር ኃይል መስመር ላይ ከፍተኛ የጥቃት ተጋላጭነት እየጨመረ መጥቷል ብለዋል።
ሚኒስትር ዴታው የተፈጠረውን ወቅታዊ የነዳጅ እጥረት ተቋቁሞ ችግሩን ለመሻገር ተቋማት ማህበረሰቡ እና ለተሽከርካሪ አስመጪዎች አማራጭ ያሉዋቸውን ምክረ ሀሳብም አቅርበዋል።
በዚህም ማህበረሰቡ አጫጭር ጉዞዎችን በኮሪደር ልማቱ በተሰሩ ምቹ የእግረኛ መንገዶችን እና የብስክሌት ተሽከርካሪዎችን እንዲጠቀሙ ጥሪ አቅርበዋል።
ሚኒስትር ዴዔታው ከአንድ ቤት እና አካባቢ የሚወጡ መኪኖዎችን የሚይዙ ሰዎች እርስ በእርስ በመተሳሰብ ቁጥራቸውን እንዲቀንሱ ጠይቀዋል። ከዚህ በተጨማሪም የኤሌክትሪክ መኪና ያላቸው ተቋማትና ግለሰቦች ቢጠቀሙ ነዳጅን መቆጠብ ይቻላል ሲሉ አስታውቀዋል።
የነዳጅ ሀብትን በቁጠባ የመጠቀም ባህል ከመቼውም ጊዜ በላይ መዳበር እንዳለበትም አሳስበዋል።
