በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ፣ ወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ከተማ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ለማድረግ ዛሬ ረፋዱን ገብተዋል። አምባሳደሩ ሁመራ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሸተ ደምለውና ሌሎች ከፍተኛ የዞኑ አመራሮች ደማቅ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
አምባሳደር ማሲንጋ ወደ አካባቢው ያቀኑት በዞኑ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ ከአመራሮቹ ጋር ለመወያየትና በስፍራው የሚገኙ የጤና ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎት ለመመልከት መሆኑ ታውቋል።
አምባሳደሩ በቆይታቸው በሰቲት ሁመራ የሚገኙ የጤና ተቋማትን የመሰረተ ልማትና የግብዓት አቅርቦት ሁኔታ በአካል ተገኝተው እንደሚጎበኙ ይጠበቃል። በተጨማሪም ከዞኑ አመራሮች ጋር በሚያደርጉት ውይይት፣ በአካባቢው ሰብአዊ ድጋፎችን ማጠናከር በሚቻልበትና ተያያዥ የልማት ስራዎች ላይ ትኩረት እንደሚያደርጉ ተገልጿል።
ይህ ጉብኝት በስትራቴጂካዊቷ የድንበር ከተማ ሁመራ ያለውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ለመረዳት እንዲሁም የአሜሪካ መንግስት በጤናው ዘርፍ የሚያደርገውን ድጋፍ ለማጠናከር ያለመ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
