የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሜዳው የሚያደርጋቸውን ጨዋታዎች በሀገሩ ለማድረግ ለካፍ ያቀረበው ጥያቄን ተከትሎ የካፍ የስታዲየም ገምጋሚ ልዑክ ባሳለፍነው ረቡዕ የካቲት 18 ወደ ድሬዳዋ ስታዲየም በማምራት የስታዲየሙን ብቁነት ከገመገመ በኋላ ኢትዮጵያ በቀጣይ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የምታደርገውን ጨዋታ እንዲያስተናግድ ጊዜያዊ ፈቃድ ሰጥቷል።
ካፍ በዛሬው ዕለት በላከው ደብዳቤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስታዲየሙን ፈቃድ እንዲያገኝ ላደረገው ጥረት እና ለገምጋሚ ቡድኑ ላሳየው ተባባሪነት ያለውን አድናቆት ገልጾ የድሬዳዋ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ለአንድ ጨዋታ ብቻ በዝግ ስታዲየም እንዲያከናውን ጊዜያዊ ፈቃድ መሰጠቱን በመግለጽ ተጨማሪ መመርያዎችን አስተላልፏል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፣ ከስታዲየሙ አስተዳደር እና የሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት በመሥራት ስታዲየሙ ፈቃድ እንዲያገኝ ከፍተኛ ጥረት የተደረገ ሲሆን ክቡር ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ ጅራ ሀገራችን በሜዳዋ ጨዋታ እንድታደርግ በካፍ የሚገኙ ኃላፊዎችን የማሳመን ሥራዎችን ሲሰሩ ቆይተው በመጨረሻም ኢትዮጵያ ከአምስት ዓመታት በኋላ የነጥብ ጨዋታ በሜዳዋ የማስተናገድ ፍቃድ ማግኘት ችላለች።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የካፍ ጊዜያዊ ፈቃድ በመገኘቱ የእግር ኳስ ወዳዱ የኢትዮጵያ ህዝብን እንኳን ደስ አለን እያለ በዚህ ሥራ ላይ ተሳትፏቸውን ላደረጉ አካላት ምስጋናውን ያቀርባል።
