የገንዘብ ሚኒስቴር የታክስ ኦዲት አፈጻጸምን እና የታክስ ስሌት ማስታወቂያ አወጣጥን የሚመራ አዲስ መመሪያ ቁጥር 1063/2017 አውጥቷል። መመሪያው በትላንትናው ዕለት ግንቦት 21 ቀን 2017 ዓ.ም. የወጣ ሲሆን፣ የታክስ አስተዳደር ሥርዓቱን ውጤታማ፣ ቀልጣፋና ግልጽ ለማድረግ ያለመ መሆኑ ተጠቁሟል።
ይህ አዲስ መመሪያ የታክስ ባለሥልጣን ባለሙያዎችንና ታክስ ከፋዮችን ኃላፊነት የሚደነግግ ሲሆን፣ በተለያዩ የታክስ ኦዲት ዓይነቶች ላይ፣ እንደ የተመላሽ ኦዲት፣ የዴስክ ኦዲት፣ ጭብጥ ተኮር ኦዲት፣ አጠቃላይ ኦዲት እና የማጭበርበር ምርመራን ጨምሮ ተፈጻሚ እንደሚሆን ይደነግጋል።
መመሪያው የፌዴራል መንግስትን የታክስ አዋጅ ድንጋጌዎች ተግባራዊ ለማድረግ የተሟላ ማዕቀፍ እንደሚሰጥ፣ እንዲሁም የኦዲት ሂደቱ ወጥነት ያለው፣ ግልጽነት የሰፈነበት እና የታክስ ከፋዮች መብት የሚጠበቅበት መሆኑን እንደሚያረጋግጥ ተመላክቷል።
የታክስ ስሌት ማስታወቂያ የሚላከው ታክስ ባልተከፈለበት፣ ተጨማሪ ታክስ እንዳለ ሲረጋገጥ፣ ወይም ታክስ ማጭበርበር ጥርጣሬ ሲኖር የተባለ ሲሆን የመስክ ኦዲት ከመጀመሩ አስር የስራ ቀናት በፊት ለታክስ ከፋዩ የጽሁፍ ማስታወቂያ መሰጠት እንዳለበት ካፒታል ከመመሪያው ለመረዳት ችሏል።
ኦዲት በሚደረግበት ጊዜ ታክስ ከፋዮች ለኦዲተሮች ምቹ ሁኔታዎችን የማመቻቸትና የሚጠየቁ ሰነዶችን የማቅረብ ግዴታ እንዳለባቸው ያሳስባል።
CapitalNews
