የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የሀገሪቱን የውጭ ንግድ ዘርፍ ለማነቃቃትና የኢንቨስትመንት ምኅዳሩን ይበልጥ ሳቢ ለማድረግ በሚል በትላትንናው ዕለት ይፋ ባደረገው መመሪያ ላኪዎች (Exporters) ከንግድ ሥራ የሚያገኙትን የውጭ ምንዛሬ ሙሉ በሙሉ (100 በመቶ) በሪቴንሽን ሂሳባቸው ውስጥ ያለምንም የጊዜ ገደብ መያዝ እንዲችሉ ተፈቅዶላቸዋል።
ከዚህ ቀደም የነበሩት የገንዘብ ይዞታ ገደቦች ሙሉ በሙሉ የተነሱ ሲሆን፣ ይህም ላኪዎች ያገኙትን ምንዛሬ ለረጅም ጊዜ እንዲያቆዩና እንደ አስፈላጊነቱ ለንግድ እንቅስቃሴያቸው እንዲጠቀሙበት ሰፊ ዕድል የሚሰጥ ነው።
ይህ አዲስ ሪፎርም በኢትዮጵያ ውስጥ የሚሠሩ የውጭ ኢንቨስተሮችንም በከፍተኛ ደረጃ የሚያበረታታ ሲሆን፣ ያገኙትን ትርፍ ያለምንም የባንክ ማረጋገጫ በቀጥታ በባንኮች በኩል ወደ ውጭ መላክ እንዲችሉ ፈቃድ ሰጥቷል።
እርምጃው ኢንቨስተሮች ያገኙትን ትርፍ ያለምንም ቢሮክራሲ ማውጣት እንዲችሉ የሚያደርግ ነው። በተያያዘም ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ያለምንም የብሔራዊ ባንክ ማረጋገጫ በባንኮች ውስጥ የውጭ ምንዛሬ ሂሳብ እንዲከፍቱ ተፈቅዶላቸዋል።
የባንክ ደንበኞችም በውጭ ምንዛሬ ሂሳባቸው ውስጥ ያለውን ገንዘብ ለራሳቸውም ሆነ ለቤተሰባቸው አባላት የትምህርት፣ የሕክምና እና የጉዞ ወጪዎችን በቀጥታ መክፈል እንደሚችሉ ብሔራዊ ባንክ አስታውቋል።
ደንበኞች ሕጋዊ ሰነዶችን ለባንካቸው በማቅረብ እነዚህን ክፍያዎች ከሂሳባቸው ላይ መፈጸም ይችላሉ። በተጨማሪም ግለሰቦች በውጭ ሀገር ለሚኖሩ ዘመዶቻቸው እስከ 3ሺህ የአሜሪካ ዶላር የሚደርስ የገንዘብ ድጋፍ በሕጋዊ መንገድ በባንኮች በኩል መላክ የሚያስችል ሥርዓት ተዘርግቷል።
