10ኛው የኢትዮ ኸልዝ ዓለም አቀፍ ጉባኤ እና ኤግዚቢሽን ሊካሄድ ነው

Date:

በአዲስ አበባ ከተማ ከመጋቢት 24 እስከ 26 ቀን 2018 ዓ.ም. የሚቆይ 10ኛው የኢትዮ ኸልዝ ዓለም አቀፍ አውደ ርዕይና ጉባኤ እንዲሁም 2ኛው የሀገር ውስጥ የሕክምና ግብዓት ምርትና ኢኖቬሽን ኤግዚቢሽን ሊካሄድ እንደሆነ ተገልጾአል።

በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ በአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት እና በፕራና ኢቨንትስ አዘጋጅነት በአዲስ ኢንተርናሽናል ኮንቬንሽን ሴንተር የሚካሄደው ይህ ዝግጅት፣ በጤናው ዘርፍ የተሰማሩ ከ90 በላይ ኩባንያዎችን በአንድ መድረክ እንደሚያገናኝ አዘጋጆቹ መጋቢት 8 ቀን 2018 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል።

በኤግዚቢሽኑ ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከስምንት ሀገራት የተውጣጡ ኩባንያዎች የሕክምና መሣሪያዎችን፣ መድኃኒቶችንና የላቦራቶሪ ግብዓቶችን ለባለሙያዎችና ለባለሀብቶች እንደሚያስተዋውቁ ተገልጾአል።

የፕራና ኢቨንትስ ፕሮጀክት ማናጀር ዶክተር ዳዊት ተስፋጊዮርጊስ እንደገለጹት፣ በጉባኤው እስከ 2 ሺህ የሚደርሱ የሕክምና ባለሙያዎች የሚሳተፉ ሲሆን በአጠቃላይ እስከ 7 ሺህ ጎብኚዎች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የኢትዮጵያ መድኃኒትና የሕክምና መገልገያ መሣሪያዎች አምራች ዘርፍ ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ታደሰ ተፈሪ በበኩላቸው፣ መድረኩ የንግድ ትስስር ለመፍጠርና የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማምጣት ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር መሳይ ወልደማርያም፣ ኤግዚቢሽኑ የሀገር ውስጥ የሕክምና ግብዓት የማምረት አቅምን ለማሳየትና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን ለመተካት የሚደረገውን ሀገራዊ ጥረት እንደሚያግዝ አስረድተዋል።

በመድረኩ ከ40 በላይ የሙያ ማጎልበቻ (CPD) ሥልጠናዎች፣ 3ኛው ለአንድ ችግር ብልህና ፈጣን የቴክኖሎጂ መፍትሄ የሚዘጋጅበት መድረጅ ወይም በእንግሊዘኛው የ‹ዲጂታል ኸልዝ ሃካቶን› እና ሳይንሳዊ ፎረሞች የዝግጅቱ አካል እንደሆኑ ታውቋል።

ያጋሩ!

መጽሔቶች

በብዛት የተነበቡ

ተጨማሪ ጽሑፎች
ተመሳሳይ

በከተማዋ ከ24 ሺህ በላይ ንቁ የግንባታ ፈቃድ ያላቸው ሳይቶች መኖራቸው ተገለፀ

በኮንስትራክሽን ዘርፍ የሚደርሰውን የህይወትና የንብረት ጉዳት ለመቀነስ የቁጥጥርና የግንዛቤ...

አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ ለሕክምና በወሰደችው መድኃኒት ምክንያት ከውድድር ታገደች

የቀድሞዋ የሁለት ጊዜ የዓለየቀድሞዋፒዮኗ ኢትዮጵያዊቷ ጉዳፍ ፀጋይ ከውድድር በፊት...

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ እውቅና ሊሰጣቸው ነዉ

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ እውቅና የሚያገኙት የጎርጎርጎረሳዉያኑ 2026 በሞሮኮ...