ኢትዮጵያ በምታዘጋጀው ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ላይ ከ45 በላይ የአፍሪካ መሪዎችን ጨምሮ እስከ 25 ሺሕ ተሳታፊዎች ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠቅ የፕላንና ልማት ሚኒስቴር አስታውቋል።
የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስዩም መኮንን እንደገለጹት፤ “የዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔዎችን ማፋጠንና የአፍሪካን የመቋቋም እና የአረንጓዴ ልማትን በገንዘብ መደገፍ” በሚል መሪ ቃል ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ሕብረት ጋር በመተባበር 2ኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 2017 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ለማካሄድ ዝግጅት በመደረግ ላይ ይገኛል።
በጉባኤው ከ45 በላይ የአፍሪካ መሪዎች እንደሚገኙና ከ20 ሺሕ እስከ 25 ሺሕ የሚሆኑ ተሳታፊዎች ይታደማሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል።
የአፍሪካ ሀገሮች የአየር ንብረትን ለመቋቋም በሚያዘጋጁት እቅድ ወደ 3 ትሪሊዮን ብር ያስፈልጋቸዋል ተብሏል።
ጉባኤው በሁለት መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር ሲሆን፤ የመጀመሪያው የአፍሪካን የአየር ንብረት ለውጥ እርምጃዎች የማሳየት፣ ሁለተኛው ደግሞ በዓለም አቀፍ ደረጃ አዳዲስ የፋይናንስ አቅሞች እንዲመጡ ማድረግ ላይ በትኩረት እንደሚመክር ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ስዩም መኮንን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ ለማጠናቀቅ 7 ኮሚቴዎችን ተዋቅሮ እንዲሁም በጠቅላላ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት የሚመራ አሰሪ ኮሜቴ፤ በፕላንና ልማት ሚኒስቴርና የአፍሪካ ሕብረት ጋር በመሆን የቅድመ ዝግጅት ሥራው እየተሰራ መሆኑ ተገልጿል።
ሚኒስትር ዴኤታው አክለውም “ጉባኤው ኢትዮጵያን ብሎም አፍሪካን በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ የመሪነት ሚናቸውን ማስጠበቅ የሚችሉበትን መንገድ ለመፍጠር እንዲሁም አፍሪካዊያን ማገኘት ያለባቸውን ጥቅም እንዲያገኙ የሚያስችል ነው” ብለዋል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
