ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ በምያንማር ታጣቂዎች እጅ የነበሩ 477 ኢትዮጵያውያን ወደ ሀገር መመለሳቸውን የቤተሰቦች ኮሚቴ እና ተመላሾች ለቢቢሲ ተናገሩ።
በአካባቢው የሚገኙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ለቀሪዎቹ 300 ገደማ ኢትዮጵያውያን የአውሮፕላን ትኬት የመግዛት አቅም እንደሌላቸው በመግለጻቸው፤ መቼ እና እንዴት ሊመለሱ እንደሚችሉ እስከአሁን እንዳልታወቀ ተገልጿል።
ታይላንድ ውስጥ ጥሩ ክፍያ ያለው ስራ እንደሚያገኙ ቃል ተገብቶላቸው ከሀገር የወጡት ኢትዮጵያውያን በታጣቂዎች እጅ ከመውደቃቸው አስቀድሞ የሳይበር ወንጀል በሚፈጸምባቸው ካምፖች ውስጥ ለግዳጅ ሰራተኝነት እና ስቃይ ተዳርገው ነበር።
ካምፖቹ የሚገኙባቸውን አካባቢዎች የሚቆጣጠሩ ታጣቂዎች የካቲት ወር ላይ ተጎጂዎችን ማስወጣት የጀመሩ ሲሆን የተወሰኑ ኢትዮጵያውያን ደግሞ አምጸው በመውጣት በታጣቂዎች እጅ ገብተዋል። ታጣቂዎች ኢትዮጵያውያኑን ጨምሮ ያስወጧቸውን የተለያዩ ሀገር ዜጎች በተለያዩ ጊዜያዊ መጠለያዎች ውስጥ አስቀምጠዋል።
በምያንማር የሚገኙት ኢትዮጵያውያን አስተባባሪ አዳነ፤ ቀሪዎቹ ተጎጂዎች የሚመለሱበትን መንገድ በተመለከተ የተስፋ “ጭላንጭል እየታየ አይደለም” ሲል ስጋቱን አጋርቷል።
