ከሩሲያ ጋር በአውዳሚ ጦርነት ውስጥ የምትገኘው ዩክሬን ከአምስት ዓመታ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የዩሊያ ስቪሪደንኮን የሀገሪቱን ጠቅላይ ሚኒስትር በማድረግ በዛሬው ዕለት ሾማለች፡፡
የሀገሪቱ ፓርላማ ከሩሲያ ጋር ይደረሳል የተባለው የሰላም ስምምነት ተስፋ እየደበዘዘ መምጣቱን ተከትሎ፤ የጦር ጊዜ አስተዳደርን ለማደስ እያከናወነ የሚገኘው ዋና የካቢኔ ማሻሻያ አካል የሆነውን የጠቅላይ ሚኒስትሯን ሹመት በ262 ድምጽ አጽድቆታል፡፡
ይህም በዩክሬን የጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ የተረከቡ ሁለተኛዋ ሴት መሪ አድርጓቸዋል፡፡
የ39 ዓመቷ የዩክሬን ጠቅላይ ሚኒስቴር ዩሊያ ስቪሪደንኮ፤ የሀገር ውስጥ የጦር መሳሪያ ምርትን የማሳደግ፣ የዩክሬንን ኢኮኖሚና ማህበራዊ አቅም የማጠናከር እንዲሁም የዩክሬናውያንን የድጋፍ ፕሮግራሞች የማስፋፋት ተልዕኮ ከፕሬዚዳንት ቮሎዲሚር ዘለንስኪ ተሰጥቷቸዋል፡፡
ዘሌንስኪ ለፓርላማ ባደረጉት ንግግር፤ አዲሱ መንግሥታቸው በዩክሬን የጦር ሜዳ ላይ ያለውን የሀገር ውስጥ መሳሪያ ድርሻ በስድስት ወራት ውስጥ ከ 40 በመቶ ወደ 50 በመቶ ያሳድጋል ብለው እንደሚጠብቁ መናገራቸውን ሮይተርስ ዘግቧል።
እ.ኤ.አ. ከ2021 ጀምሮ ተቀዳሚ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የኢኮኖሚ ሚኒስትር ሆነው ያገለገሉት የዩሊያ ስቪሪደንኮ በበኩላቸው ከሹመታቸው በኋላ ባደረጉት ንግግር፤ “በፍጥነት እና በቆራጥነት” ለመስራት ቃል ገብተዋል።
በኤክስ ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍም፤ “ጦርነት ለመዘግየት ቦታ አይሰጥም” ሲሉ ጽፈዋል።
“ለመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት ቅድሚያ የምንሰጣቸው ጉዳዮች ግልጽ ናቸው፡፡ ለሠራዊቱ አስተማማኝ አቅርቦት፣ የአገር ውስጥ የጦር መሣሪያ ምርትን ማስፋፋት እና የመከላከያ ሰራዊታችንን የቴክኖሎጂ ጥንካሬ ማሳደግ ናቸው” ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ስቪሪደንኮ የዩክሬን ማዕድን ሀብት ለአሜሪካ የሚሰጥ ስምምነት ላይ በመደራደር በትራምፕ አስተዳደር ዘንድ በደንብ የሚታወቁ ሲሆን፤ ይህም በኪዬቭ እና በዋሽንግተን መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር ወሳኝ ስለመሆኑ ተመላክቷል።
(አሐዱ ሬዲዮ)
