የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሀገሪቱ የኢሚግሬሽን እና የጉምሩክ አስከባሪ ተቋም ወይም በምህጻረ ቃሉ ICE ላይ ያልተጠበቀ የስም ለውጥ ለማድረግ ማቀዳቸውን ይፋ አድርገዋል።
ፕሬዝዳንቱ በማህበራዊ ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ተቋሙ ከእንግዲህ በኋላ “National” የሚል ቃል ተጨምሮበት NICE (National Immigration and Customs Enforcement) ተብሎ እንዲጠራ የቀረበላቸውን ሀሳብ በሙሉ ድምፅ ደግፈዋል።
ይህ የታቀደው የስም ለውጥ ከቀላል ስያሜ ባለፈ ትልቅ የሚዲያ ስትራቴጂን ያነገበ ነው። ስያሜው ወደ “NICE” ከተቀየረ ተቋሙን የሚተቹ የዜና አውታሮች እና ጋዜጠኞች ሳይቀሩ ስለ ተቋሙ ሰራተኞች ሲዘግቡ “NICE agents” ወይም “ደግ ወኪሎች” የሚለውን ቃል ለመጠቀም እንደሚገደዱ ታስቧል።
ይህም በተቋሙ ላይ የሚሰነዘሩ አሉታዊ ዘገባዎችን በቃላት ጨዋታ ለመቀልበስ እና በህዝብ ዘንድ ያለውን ገጽታ ለማለስለስ ያለመ እንደሆነ ተነግሯል።
ምንም እንኳን ፕሬዝዳንት ትራምፕ ለውጡ በአስቸኳይ ተግባራዊ እንዲሆን ትዕዛዝ ቢሰጡም ጉዳዩ በቀጥታ ወደ ስራ ከመግባቱ በፊት የሀገሪቱን የህግ መወሰኛ ምክር ቤት ይሁንታ ማግኘት ይኖርበታል።
በአሁኑ ወቅት ይህ ጉዳይ በአሜሪካ ፖለቲካ ውስጥ ትልቅ መነጋገሪያ ሆኖ የቀጠለ ሲሆን ደጋፊዎቻቸው የፕሬዝዳንቱን ብልህነት የሚያሳይ ነው ሲሉ ተቃዋሚዎች ደግሞ መሰረታዊ የፖሊሲ ለውጥ ከማድረግ ይልቅ በቃላት መደበቅ ነው በሚል እየተቹት ይገኛሉ።
