የአፍሪካ ግዙፉ አየር መንገድ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ የሀገር ውስጥ እና የጎረቤት ሀገራትን የበረራ መዋቅር ይበልጥ ለማስፋፋት የሚያስችሉትን 25 ትናንሽ የንግድ አውሮፕላኖችን ለመግዛት በሚቀጥሉት ሦስት ወራት ውስጥ የመጨረሻ ውሳኔ ላይ እንደሚደርስ አስታወቀ።
የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው በብራዚል ሪዮ ዲ ጄኔሮ እየተካሄደ ባለው የዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማኅበር (IATA) ዓመታዊ ጉባኤ ላይ እንደገለጹት፣ በአሁኑ ወቅት 147 አውሮፕላኖችን እያበረረ የሚገኘው ተቋማቸው ለዚህ ግዥ ሦስት አማራጮችን እያጠና ነው።
አየር መንገዱ አይኑን የጣለባቸው አውሮፕላኖች የኤርባስ A220፣ የብራዚሉ ኤምብራየር E-2 እና በዘንድሮው ዓመት በአሜሪካ የፌደራል አቪዬሽን ባለሥልጣን (FAA) ይፋዊ ዕውቅና ያገኛል ተብሎ የሚጠበቀውን የቦይንግ 737 MAX 7 ሞዴሎችን እንደሆነ የሮይተርስ ዘገባ ያመለክታል።
ዋና ሥራ አስፈጻሚው ምንም እንኳ ውሳኔውን ለማሳለፍ የተወሰኑ መፈታት ያለባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም፣ በሚቀጥሉት ሦስት ወራት ውስጥ ግን አሸናፊው አምራች ተለይቶ ይታወቃል ብለዋል።
በሌላ በኩል፣ አየር መንገዱ በአሁኑ ወቅት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ባለው ጦርነት ሳቢያ ለጄት ነዳጅ የሚያወጣው ወጪ በ60% ገደማ ማደጉን አቶ መስፍን ገልጸዋል። የነዳጅ አቅርቦት እጥረትን በተሳካ ሁኔታ መፍታት ቢቻልም፣ የዋጋው መናር ግን አሁንም ትልቅ ፈተና መሆኑን ጠቁመዋል።
