የኢትዮጵያ ትራንስፖርት አሠሪዎች ፌዴሬሽን፤ አዲሱን የጉምሩክ አዋጅ ለማስፈጸም የሚወጣው መመሪያ የባለንብረቶችን ሥጋት ከግምት ውስጥ እንዲያስገባ ጠይቋል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 2 ቀን 2018 ዓ.ም. ያጸደቀው አዋጅ ቁጥር 1425/2018፤ በሕገ-ወጥ መንገድ (ኮንትሮባንድ) አገር ውስጥ የገባ ማንኛውም ዕቃ የተገኘበት ተሽከርካሪ እንደሚወረስ ይደነግጋል።
የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃኔ ዘርዑ እንደገለጹት፤ ድንጋጌው ባለቤቱ ሳያውቅ በአሽከርካሪው በሚፈጸም ጥፋት ምክንያት ባለንብረቱ እንዲጎዳ የሚያደርግ በመሆኑ ከፍተኛ ሥጋት ፈጥሯል።
ይህ አሠራር ባለንብረቶችን ለኪሳራ የሚዳርግ በመሆኑ፣ በቀጣይ በሚወጡ መመሪያዎች ላይ ታሳቢ እንዲደረግ ጠይቀዋል።
የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዶክተር ሞላ ዓለማየሁ በበኩላቸው፤ ማስፈጸሚያ መመሪያዎች በጥናት ላይ የተመሠረቱ ካልሆኑ በኢኮኖሚው ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ይኖራቸዋል ብለዋል።
ደንቦቹ ባለሀብቶች ከትራንስፖርት ዘርፉ እንዲርቁ ሊያደርጉ እንደሚችሉ አክለው ሥጋታቸውን ገልጸዋል።
ባለሙያዎቹ፤ አዋጁ ሕገ-ወጥ ንግድን ለመቆጣጠር ቢረዳም፣ መመሪያዎቹ ግልጽነት እና ተጠያቂነትን ባረጋገጠ መልኩ እንዲዘጋጁ ጠይቀዋል። አፈጻጸሙ የባለቤቶችን መብት በሚጠብቅ እና የንግድ እንቅስቃሴን በማያስተጓጉል መንገድ መዘጋጀት እንዳለበትም አጽንኦት ሰጥተዋል።
