የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር እና የአግራ (AGRA) የቦርድ ሰብሳቢ ኃይለማርያም ደሳለኝ የዓለም ትልቁ የግብርና ምርምር ሽርክና የሆነው የሲጂአር (CGIAR) ቦርድ የመጀመሪያ ሰብሳቢ ሆኖ መሾማቸው ተገለጸ።
ይህ ሹመት ሳይንስን ከአርሶ አደሮች የዕለት ተዕለት ሕይወት ጋር በማስተሳሰር ረገድ አፍሪካንና ዓለምን ለመምራት የሚደረገውን ጥረት የሚያጠናክር ትልቅ ምዕራፍ መሆኑ ተመላክቷል።
አቶ ኃይለማርያም ከ2019 ጀምሮ የአግራ (AGRA) ቦርድን በመምራት በነበራቸው ቆይታ አመርቂ ሥራዎችን ያከናወኑ ሲሆን፣ ቀደም ሲልም እንደ ኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የአፍሪካ ኅብረት ሊቀመንበር በመሆን ያሳዩት ጠንካራ መሪነት ለአህጉሪቱ የግብርና እና የአየር ንብረት አጀንዳዎች መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል።
የአግራ እና የሲጂአር ተቋማት ሳይንሳዊ ምርምሮችን ወደ መሬት በማውረድና ለአነስተኛ አርሶ አደሮች ተደራሽ በማድረግ ረገድ ያላቸውን የትብብር መሠረት ይህ ሹመት ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ተገልጿል።
