ትናንት ሀሙስ ጠዋት ለተፈፀመው ለዚህ ግድያ የኬንያ ባለስልጣናት በኢትዮጵያ የሚገኙትን የሙርሌ ጎሳዎች ተጠርጣሪ አድርገዋል፡፡ የአካባቢው አስተዳዳሪ ሙስጠፋ ኬቦ ግድያው መፈፀሙን አረጋግጠው የሞቱን በቱርካና ሀይቅ አሳ አስጋሪዎች መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
አሳ አስጋሪዎቹ ስራቸውን ካከናወኑ በኋላ በተኙበት ይህ ጥቃት ተፈፅሞባቸዋል የሚል ግምት እንዳላቸውም አስታውቀዋል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች የተኩስ እሩምታ መስማታቸውን እንደተናገሩና ጥቃቱን የፈፀሙት ከኢትዮጵያ የመጡ የሙርሌ ጎሳ አባላት መሆናቸውን እንደገለፁም አስረድተዋል፡፡
በቱርካና ሀይቅ አሳ ማስገር መብት የተነሳ የኬንያው ቱርካናና የኢትዮጵየው ዳሳነች ጎሳዎች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከፍተኛ ውዝግብ ውስጥ መግባታቸው ይታወቃል፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት በዚሁ ውዝግብ የተነሳ ከ20 በላይ ኬንያዊያን መገደላቸው መዘገቡም አይዘነጋም፡፡ የኬንያው ፕሬዝደንት ዊልያም ሩቶ ይህንን አካባቢ በሚቀጥለው ወር ለመጎብኘትና ያለውን ውዝግብ በቅርበት ለመመልከት ማቀዳቸውን ዘገባዎች አስታውቀዋል፡፡
(ዘ-ሐበሻ ዜና)
