የአዲስ አበባ ከተማ የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ከሚቀጥለው በጀት ዓመት ጀምሮ እንደ ልደት እና ሞት ያሉ የወሳኝ ኩነት ምዝገባዎችን በወቅቱ በማያስመዘግቡ ነዋሪዎች ላይ የ5 ሺሕ ብር ቅጣት ሊጥል እንደሚችል አስታውቋል።
የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ጥጋቡ ሹመይ የማኅበረሰቡን የግንዛቤ ማነስ ከግምት ውስጥ በማስገባት እስካሁን አስገዳጅ የቅጣት ውሳኔዎች ሳይተላለፉ እንደቆየም ተናግረዋል።
ሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ምዝገባውን በወቅቱ ባላደረጉ ነዋሪዎች ላይ ቅጣቱ ተግባራዊ ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል።
ማንኛውም ነዋሪ ልደትን በ90 ቀናት ውስጥ ፍቺ፣ ጋብቻ፣ ሞት እና ጉድፈቻ ኩነቶችን ደግሞ በ30 ቀናት ውስጥ ማስመዝገብ ግዴታ አለባቸው ብለዋል።
ነዋሪዎች በተቀመጠው የጊዜ ቀነ-ገደብ በአግባቡ በመጠቀም ራሳቸውን ካልተፈለገ የገንዘብ ቅጣት እንዲጠብቁም ኤጀንሲው አሳስቧል።
በተያዘው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ ልደት 83 ሺሕ 767፣ በሞት 5 ሺሕ 161 እንዲሁም በጉድፈቻ 178 መመዝገባቸውን አቶ ጥጋቡ ሹመይ ገልጸዋል።
በአጠቃላይ 89 ሺሕ 106 የወሳኝ ኩነት ምዝገባ መደረጉን ተናግረዋል።
የሲቪል ምዝገባ አሠራርን ማዘመን ለሀገራዊ ዕቅድና ለከተማዋ የሕዝብ ቁጥር ሚዛን ወሳኝ በመሆኑ ነዋሪዎች ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።
አሐዱ ራዲዮ
