የኤርትራ ብሔራዊ ቡድን ለ2019 (እ.ኤ.አ 2027) የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ታሪካዊ በሆነ ሁኔታ ለምድብ ድልድል ካለፈ በኋላ፣ ሰባት ተጫዋቾች ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ፈቃደኛ ሳይሆኑ በደቡብ አፍሪካ መቅረታቸውን ቢኤስኤን ስፖርትስ ዘግቧል።
ይህ ክስተት የተሰማው ኤርትራ በድምር ውጤት ኤስዋቲኒን 4 ለ 1 በሆነ ውጤት በማሸነፍ፣ ከ19 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የምድብ ድልድል መሸጋገሯን ካረጋገጠች ጥቂት ቆይታ በኋላ ነው።
እንደ ዘገባው ከሆነ ለጨዋታው ወደ ደቡብ አፍሪካ ከተጓዙት አሥር በአገር ውስጥ የሚጫወቱ ተጫዋቾች መካከል ወደ ኤርትራ የተመለሱት ሦስቱ ብቻ ናቸው። ወደ ሀገራቸው የተመለሱት ተጫዋቾች አብሌሎም ተክለዝጊ፣ ናሆም ታደሰ እና ሮሜል አብዱ ሲሆኑ፣ ቀሪዎቹ ሰባት ተጫዋቾች በደቡብ አፍሪካ መቅረታቸው ተነግሯል።
ይህ ድርጊት የኤርትራ ስፖርተኞች ለዓለም አቀፍ ውድድሮች ወደ ውጭ ሀገራት በሚጓዙበት ወቅት የግል እና ፖለቲካዊ ምክንያቶችን በመጥቀስ በዚያው የመቅረት (ጥገኝነት የመጠየቅ) ልማዳቸው ላይ አዲስ ስጋትን ፈጥሯል።
ኤርትራ ወደ ምድብ ድልድሉ ማለፏ ለሀገሪቱ የእግር ኳስ እድገት ትልቅ ስኬት ተደርጎ ሲወደስ የቆየ ቢሆንም፣ የተጫዋቾቹ ድንገተኛ መሰወር ለቡድኑ ከፍተኛ እንቅፋት እንደሚሆን ተገልጿል።
