የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤ በዓለም ዙሪያ በክርስቲያኖች ላይ የሚፈጸሙ ስደት፣ ግድያ እና እገታዎችን በመጥቀስ፣ በአሁኑ ወቅት ክርስትና በከፍተኛ ሁኔታ እየተገለለ መሆኑን ገለፁ።
ፓትርያርኩ የገና በዓልን እና የፈረንጆቹን ዘመን መለወጫ አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክታቸው፤ የቴክኖሎጂ እድገትንና ቁሳዊ ምቾትን ጨምሮ ዘመናዊው ስልጣኔ ያስመዘገባቸውን ውጤቶች እውቅና ተሰጥተዋል። ሆኖም ግን ይህ ስልጣኔ ለክርስትና እምነት የማይመችና ፈታኝ ሁኔታን መፍጠሩንም ጠቁመዋል።
“በዓለም ላይ ቁጥሩ ከፍተኛ የሆነ ሕዝብ ክርስትናን የሚከተል ቢሆንም፣ በዘመናችን ግን ክርስትና በተለያዩ ምክንያቶች ወደ ጎን እየተገፋ መሆኑን እያየን ነው” ብለዋል ቅዱስነታቸው።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ስላለው ስቃይ፣ እገታ እና ግድያ ያላቸውን ጥልቅ ስጋት ገልጸዋል። እነዚህ ድርጊቶች ስልጣኔ አከብራቸዋለሁ ከሚላቸው የሥነ-ምግባር እሴቶች ጋር የሚቃረኑ መሆናቸውንም አስረድተዋል። አያይዘውም፣ አውቀውም ይሁን ሳያውቁ ክርስትናን ለማዳከም የሚሰሩ አካላት “ከክፉ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ” አሳስበዋል።
ፓትርያርኩ በመልዕክታቸው ዓለም አቀፍ ተቋማት እና የሚመለከታቸው አካላት “የሃይማኖት ነፃነትን ለመጠበቅ” ተግባራዊ እርምጃዎችን እንዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል። እምነትን የመከተል መብት ሊከበር እና ሊጠበቅ የሚገባው መሰረታዊ ሰብአዊ መብት መሆኑንም አፅንዖት ሰጥተው ገልጸዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ መልዕክታቸውን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ካለው መንፈሳዊ ትርጓሜ ጋር በማያያዝ፤ የክርስቶስ ልደት ሰማይና ምድርን አንድ ያደረገ እና የሰውን ልጅ ወደ ሰላም የጠራ መለኮታዊ መገለጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤ አዲሱ ዓመት እንደ ቀን ለውጥ ብቻ ሳይሆን ምስጋና እንደሚገባው መለኮታዊ ስጦታ ተደርጎ ሊታይ እንደሚገባም አክለው ገልጸዋል።
ቅዱስነታቸው በተጨማሪም፤ እስራኤልና ፍልስጤምን እንዲሁም ሩሲያና ዩክሬንን ጨምሮ በግጭት በሚታወኩ ቀጠናዎች ሰላም እንዲሰፍን ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፤ በሰቪሎች ላይ የሚፈጸመውን ግድያ፣ ስቃይ እና መፈናቀል አውግዘዋል። ፓትሪያርኩ ከስደተኞች እና ከተጎዱ ማህበረሰቦች ጋር አንድነት እንዲኖርም ጥሪ አቅርበዋል።
አቡነ ማትያስ መልዕክታቸውን ሲያጠቃልሉም፤ የተራቡ የሚጠግቡበት፣ ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው የሚመለሱበት፣ ልዩነቶች በዕርቅ የሚታረቁበት፣ ጦርነቶች የሚቆሙበት፣ ሰብአዊ ክብር የሚመለስበት እና ፍቅር በሁሉም የሰው ልጅ ዘንድ የሚዳረስበት ፍትሃዊ እና ርኅራኄ የሰፈነበት ዓለም እንዲሆን ተመኝተዋል።
