አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡና የሚወጡ መርከቦችን ለማገድ የባሕር ላይ ከበባ እንደምታደርግ ማስታወቋን ተከትሎ፤ ሰኞ ሚያዝያ 05 ቀን 2018 ዓ.ም. በማለዳው የገበያ ግብይት የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳይቷል።
አልጀዚራ እንደዘገበው፤ የአሜሪካ ድፍድፍ ነዳጅ (US crude oil) ዋጋ 8 በመቶ በመጨመር በአንድ በርሜል 104.24 ዶላር ደርሷል።
የዓለም አቀፍ መለኪያ የሆነው የብሬንት (Brent) ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋም በ7 በመቶ ጭማሪ በማሳየት በበርሜል 102.29 ዶላር ሆኖ ተመዝግቧል።
ዓለማቀፉ ግዙፍ የኢነርጂ ገበያ ተንታኝ ኦኒክስን (Onyx) ዋቢ በማድረግ ብሉምበርግ እንደዘገበው ደግሞ፤ አሜሪካ የባሕር ላይ ከበባውን የምትቀጥል ከሆነ ዓለማቀፍ የነዳጅ ዋጋ እስከ 150 ዶላር ሊያሻቅብ ይችላል።
የአሜሪካና የእስራኤል ጥቃት በኢራን ላይ በየካቲት 21 ቀን 2018 ዓ.ም. ከመጀመሩ በፊት፤ በአንድ በርሜል 70 ዶላር ገደማ ይሸጥ የነበረው የብሬንት ነዳጅ ዋጋ፤ ጦርነቱ ከተጀመረ በኋላ፤ ከፍተኛ መዋዠቅ የታየበት ሲሆን፤ በአንድ በርሜል እስከ 119 ዶላር ደርሶ እንደነበር ይታወሳል።
ባለፈው ሳምንት ዓርብ ሚያዝያ 03 ቀን 2018 ዓ.ም. አሜሪካ እና ኢራን በፓኪስታን ንግግር ከማድረጋቸው በፊት፤ ለሰኔ ወር የሚቀርብ የብሬንት ነዳጅ ዋጋ በ0.8 በመቶ ቀንሶ በበርሜል 95.20 ዶላር ነበር።
አሜሪካ የኢራን ወደቦችን ለመዝጋት ማቀዷን ተከትሎ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አሳየ
Date:
